የኢትዮጵያ የብሮድካስት ባለስልጣን ለሶስት አዳዲስ የንግድ የኤፍኤም ራዲዮ ፈቃድ ለመስጠት የሚያስችለውን ጨረታ አወጣ፡፡

የካቲት ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ወገኖች ጨረታው ለይስሙላ የወጣ መሆኑንና የሚሰጣቸው ሰዎች አስቀድመው የተዘጋጁ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡

ባለስልጣኑ አስካሁን ራዲዮ ፋናን ጨምሮ ለአራት ያህል የንግድ ኤፍኤም ጣቢዎች ፈቃድ የሰጠ ሲሆን የረጅም ሞገድ ራዲዮ ጣቢያ እና የግል ቴሌቭዥን ጣቢያ ፈቃድ መስጠት በአዋጅ ቁጥር 533/1999 ስልጣን የተሰጠው ቢሆንም እስካሁን ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኝነት ሳይታይበት ቀርቶአል፡፡

ባለስልጣኑ ባለፉት ጊዜያት በተመሳሳይ መልኩ ጨረታ አውጥቶ መንግስትን ለሚደግፉ ወገኖች ብቻ ፈቃድ ሰጥቶአል በሚል ትችት ሲቀርብበት የቆየ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ያወጣውና እስከ መጋቢት 24 ለተጫራቾች ክፍት ሆኖ በሚቆየው ጨረታ ላይም ተመሳሳይ ድርጊት መከሰቱ አጠራጣሪ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡

የካቲት 25 ቀን 2006 ኣ.ም በአዲስ ዘመን ጋዜጣ በወጣው በዚሁ ጨረታ ለሶስት ኤፍኤም ራዲዮ ጣቢዎችን በአዲስአበባ፣አንድ ደግሞ በአዋሳ ፈቃድ ለመስጠት ዝግጅት ማድረጉን ባለስልጣኑ አስታውቋል፡፡

በ1999 ኣ.ም የወጣው የብሮድካስት አዋጅና በሁዋላም የተሸሻለው አዋጅ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች ጭምር ኢትዮጽያዊን ማቋቋም እንደሚችሉ የደነገገ ቢሆንም አገሪቱ ለዚህ ወግ አልበቃችም በሚል ሰንካላ አስተሳሰብ ፓርላማው ያወጣውን ህግ በባለስልጣኑ መጣሱ ተደጋግሞ መዘገቡ የሚታወስ ነው፡፡