የኢትዮጵያ አየር መንገድ አዲስ የስምሪት ሃላፊ ሾመ

የካቲት ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ረዳት ካፒቴን ሃይለመድህን አበራ የኢትዮጵያን አየር መንገድ ንብረት የሆነውን ቦይንግ 767 በመጥለፍ ጄኔቫ በማሳረፍ ጥገኝነት መጠየቁን ተከትሎ፣ ካፒቴን ዮሃንስ ሃይለማርያምን አዲስ የስምሪት ሃላፊ አድርጎ ሾሟል።

የቀድሞው ሃላፊ ካፒቴን ደስታ ዘሩ ስልጣናቸውን በምን ሁኔታ እንደለቀቁ ባይታወቅም፣ ስልጣናቸውን የለቀቁት በጠለፋው ማግስት መሆኑ ጉዳዩ ከሃይለመድህን አበራ ጠለፋ ጋር ሳይያያዝ አይቀርም የሚሉ አስተያየቶች ይቀርባሉ።

በሌላ በኩል የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ ተወልደ ገብረማርያም ጠለፋው የአየር መንገዱን ስም በምንም መልኩ እንዳልጎዱት ተናግረዋል። የስዊስ አቃቢ ህጎች በረዳት ፓይለት ሃይለመድህን ላይ የሚያደርጉትን የምርምራ ውጤት ይፋ ሳያደርጉ ፣ የአየር መንገዱ ስራአስኪያጅ በየትኛው ጥናት ላይ ተመስርተው “ጠለፋው ምንም አይነት ተጽኖ አላመጣም” ብለው እንደተናገሩ ግልጽ አላደረጉም።

አቶ ተወልደ ከጠለፋው ጋር የተያያዙ ችገሮችን በብቃት መፍታታቸውንም ተናግረዋል፣ ይሁን እንጅ የትኛውን ችግር እንደፈቱ አላብራሩም።

የረዳት ካፒቴን ሃይለመድህን አበራ ጠለፋ የመገናኛ ብዙሃንን እና የኢትዮጵያውያንን ስሜት እንደያዘ ነው። በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ለአብራሪው ድጋፋቸውን በተቃውሞ ሰልፎች እየገለጹ ነው። በስዊዘርላንድ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ሃይለመድህን እንዲፈታ የድጋፍ ፊርማ ማሰባሰብ ጀምረዋል።