የኢትዮጵያ መንግስት እስክንድር ነጋ የታሰረው በአሸባሪነቱ እንጅ በጋዜጠኝነቱ አይደለም ሲል ለአውሮፓ ህብረት መልስ ሰጠ

መጋቢት ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-የኢህአዴግ አገዛዝ በእስር ላይ የሚገኘውን እውቁን ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን በተመለከተ  ከአውሮፓ ህብረት የፓርላማ አባላት ለቀረበት ጥያቄ በጽሁፍ በሰጠው መልስ ” እስክንድር ነጋ የጋዜጠኛነት ስራውን በመስራቱ ሳይሆን አሸባሪ ድርጅቶችን ሲረዳ በመገኘቱ ነው” የተፈረደበት ብሎአል።

እስክንድር ነጋ በህቡእ ከሚንቀሳቀሰው ግንቦት7 ከተባለው ድርጅት ጋር ግንኙነት እንደነበረው፣  ከኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ እየሰረጉ ለሚገቡ አሸባሪዎች ስልጠና ይሰጥ እንደነበርና ከኤርትራና ከግንቦት7 መሪዎችንም በስውር ያገኛቸው እንደነበር” ገልጿል።

የኢትዮጵያ መንግስት ለአውሮፓ ህብረት የፓርላማ አባላት የሰጠው መልስ እጅግ አሳፋሪ ነው ሲል አንድ ታዋቂ ጋዜጠኛ አስተያየቱን አስፍሯል።

በቅርቡ 30 የሚሆኑ የአውሮፓ ህብረት በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ላይ ለመነጋገር ወደ አዲስ አበባ ማቅናታቸውን መዘገባችን ይታወሳል።

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የ2012 የፔን አሜሪካን ሴንተር ፍሪደም ቱ ራይት ተሸላሚ መሆኑ ይታወሳል። የጋዜጠኛ እስክንድ ነጋ ባለቤት ሰርካለም ፋሲል ከምርጫ 97 ጋር በተያያዘ ከአንድ አመት ለ8 ወራት ያክል ጊዜ መታሰሩዋ እና በእስር ቤትም የመጀመሪያውን ወንድ ልጃቸውን ናፍቆት እስክንድርን መውለዷ ይታወቃል።