የኢህአዴግ ቡድን የአቶ መለስን ሞት ለፖለቲካ ዘመቻ መጠቀሙ እንዳሳፈራቸው አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ተናገሩ

ነሀሴ ፳፱ (ሀያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የኦሮሞ ፌደራሊስ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ የበላይ ጠባቂና የቀድሞ የፓርላማ አባል የነበሩት አቶ ቡልቻ ፣ አቶ መለስ ዜናዊ እንደ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎች ዲክታተር ነበሩ ብለዋል::

የኢህአዴግ ቡድን የአቶ መለስን ሞት ለፖለቲካ ፍጆታ ማዋል ኢስነምግባራዊ እና የሚዘገንን ነው በማለት መላውን የኢህአዴግ አመራሮች ወቅሰዋል ::

ኢህአዴግ ህዝቡን አልቅሱ ብሎ አለማስገደዱን ይልቁንም በራሱ ፈቃድ ፈንቅሎ እንደወጣ ይናገራል ተብለው ለተየጠቁት አቶ ቡልቻ፣ ኢህአዴግ በህዝብ ሀብት በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በግልጽ ቅስቀሳ ያደርግ እንደነበር ጠቅሰዋል ::

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአሜሪካ ልኡክ የሆኑት ሱሳን ራይስ ለአቶ መለስ የሰጡት ምስክርነት የግል ስሜትን ከመንግስት አቋም ጋር የቀላቀለ ነው ብለው እንደሚረዱት አቶ ቡልቻ ተናግረዋል::

አንድ ቡድን ስልጣኑን ይዞ ለመቀጠል የሚያስብ ይመስላል የሚሉት አቶ ቡልቻ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ስሜቱን እንዲገልጥ ሊፈቀድለት ይገባል ሲሉ መክረዋል::