የአፍሪካ ቢሊየነሮች ቁጥር ቀነሰ

 (ኢሳት ዲሲ–ጥር 7/2011)በአፍሪካ የቢሊየነሮች ቁጥር ከ23 ወደ 20 መውረዱን ፎርብስ ዘገበ።

የባለጸጎቹን የሃብት መጠን በተመለከተ በየዓመቱ ደረጃ የሚያወጣው ፎርብስ በሳምንቱ መጨረሻ በለቀቀው ሪፖርት ናይጄሪያዊው አሊኮ ዳንጉቴ በ10.3 ቢሊየን ዶላር አሁንም የአፍሪካ ግንባር ቀደም ሃብታም ቢሆኑም ሃብታቸው ከቀደመው ዓመት ወደ 2 ቢሊዮን ዶላር ቀንሶ ተገኝቷል።


አሊኮ ዳንጎቴ በኢትዮጵያ የሚገኘው ዳንጎቴ ሲሚንቶ ፋብሪካ ባለቤት መሆናቸውም ይታወቃል።

ከዓመት በፊት የዚሁ ፋብሪካ ስራ አስኪያጅና ሌሎች የድርጅት ሰራተኞች ባልታወቁ ታጣቂዎች አዲስ አበባ አቅራቢያ መገደላቸው አይዘነጋም።

አሊኮ ዳንጎቴ በአፍሪካ ግንባር ቀደም ባለጸጋ ሲሆኑ ሁለተኛ ባለጸጋ የሆኑትም ናይጄሪያዊው ማይክ አዶንጋ ሲሆኑ የሃብታቸው መጠንም 9.2 ቢሊየን ዶላር ነው።

ማይክ ኦዶንጋ አምና የነበራቸውን የ5.3 ቢሊዮን ዶላር ሃብት በዓመት ግዜ ወደ 9.2 ቢሊየን ዶላር ማሳደጋቸውም ተመልክቷል።

የአፍሪካ ባለጸጋነትን ደረጃ በ3ኛነት የያዙት ደቡብ አፍሪካው ኒኪ ኦፕንሒሟር ሲሆኑ የሃብታቸው መጠን 7.3 ቢሊየን ዶላር እንደሆነም ተጠቅሷል።

በአጠቃላይ ከ20ዎቹ የአፍሪካ ቢሊየነሮች 5ቱ ግብጻውያን እንዲሁም ሌሎች 5 ደቡብ አፍሪካውያን ናቸው።

ናይጄሪያ 4 እንዲሁም ሞሮኮ 2 ቢሊየነር ሲኖራት አልጄሪያ፣ አንጎላ እንዲሁም ታንዛኒያና ዚምባቡዌ እያንዳንዳቸው አንድ አንድ ቢሊየነር አስመዝግበዋል።

አምና በቢሊየነር ዝርዝር ውስጥ የነበሩትና ዘንድሮ ከስረው ሃብታቸው ቢሊየን ዶላር መጠጋት ያልቻለው ባለሃብቶች ሶስቱም የደቡብ አፍሪካ ተወላጆች መሆናቸውን መረጃው አመልክቷል።

ይህ የአፍሪካ ቢሊየነሮች ዝርዝር በትውልድ ሱዳናዊ በዜግነት እንግሊዛዊ የሆኑትን ዶ/ር መሃመድ ኢብራሂም (ሞ ኢብራሂም) እንዲሁም በዜግነት ሳውዲ አረቢያ የሆኑትን ትውልደ ኢትዮጵያዊ ሺህ መሃመድ አልአላሙዲንን በአፍሪካ ዝርዝር ውስጥ አላስገቡም።

ላለፉት 15 ወራት ያህል በሳውዲ አረቢያ በእስር ቤት የሚገኙት መሃሙድ አላሙዲና የሌሎቹ የሳውዲ ባለጸጎች የሃብት ሁኔታ በቂ መረጃ ባለመኖሩ ከቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ መሰረዛቸው ታውቋል።

በዓለማችን ያሉ ቢሊየነሮች በአጠቃላይ 2ሺህ 208 መሆናቸውም ተመልክቷል።

እነዚህ የ72 ሃገራት ዜጎች ሲሆኑ 585 ቢሊየነር በመያዝ አሜሪካ ቀዳሚ ስትሆን ቻይና በ373 ቢሊየነሮች ሁለተኛውን ስፍራ ይዛለች።

የዓለማችን ቁጥር አንድ ባለጸጋ ጄፍ ቢዞ በ136 ቢሊየን ዶላር በቁንጮነት ተቀምጧል።