የአገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ ተመልክቶ የቀረበው እቅድ ተቃውሞ ገጠመው

የአገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ ተመልክቶ የቀረበው እቅድ ተቃውሞ ገጠመው
(ኢሳት ዜና ማጋቢት 04 ቀን 2010 ዓ/ም) የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤ አቶ ያለው አባተ፣ የተወካዮች ምክር ቤት ም/አፈጉባኤ ወ/ሮ ሽታዬ ምናለ፣ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አማኑኤል አብርሃም ፣ አቶ አጽብሐ አረጋዊ ፣ የሰብአዊ መብት ዳይሬክተር ዶ/ር አዲሱ ገብረእግዚአብሔር በተገኙበት የወቅቱን የሀገሪቱን ሁኔታ ተመልክቶ በአገዛዙ የቀረበው ስምንት ነጥቦችን የያዘው የእቅድ ዝርዝር ተቃውሞ አጋጥሞታል።
በስብሰባው ላይ ከተሳተፉት መካከል አንድ ሴት ተናገሪ “ከመድረክ እንደቀረበው ሳይሆን በአሁን ጊዜ ለሀገራችን ወቅታዊ ችግር ያበቃን የተደራጀ ፀረ ሰላም ሃይል ተፈጥሮ አይደለም፣ ትልቁ ችግር የራሳችንን ችግር ነው። ይህንን ለምን እንደብቃለን? ለሀገር ይጠቅማል ብለን አንድ ጉዳይ ስናነሳ የተቃዋሚ ፓርቲ ሃሳብ እና አቋም ነው ተብለን እንድንሸማቀቅ እንደረጋለን። ይሄ ችግር እያለ ፀረ ሰላም ሃይሎች ብለን መፈረጃችንን አግባብነት የለውም” ብለዋል።
ሌላው ተናጋሪ ደግሞ “ የመንግስት አመራሮች ብቃት ራሱ አጠያያቂ ነው ። ብቃታቸው በደንብ መፈተሽ አለበት ። አመራሮቹ ሁል ጊዜ የውጭ ሃይሎች ሴራ ነው እያሉ እስከመቼ ያደበሰብሳሉ? አንድ የመከላከያ አባል በምን ሚዛን፣ በምን ዳኝነት ነው መሳርያ ባልታጠቁ ዜጎቹ ላይ ጥይት የሚያርከፈክፈው? ሰራዊታችን ሕዝባዊ ነው እየተባለ በየመድረኩ የሚነገረው በጣም ስህተት ነው። መቶ በመቶ ሕዝባዊ አይደለም “ ሲል ገልጸዋል።
ሌላው ተናጋሪ ደግሞ “ ዛሬ የተሰበሰብነው በነገው እለት ከመላው ሰራተኛ ጋር በሚኖረን የጋራ ስብሰባ ለሚነሱ ጥያቄዎች መልስ እንድንሰጥ ታስቦ ነው። ሆኖም ግን የየመስርያ ቤታችን ሰራተኞች ለሚያነሱት ጥያቄ እንዴት ብለን የወቅቱን ሁኔታ ተመርኩዘን መልስ እንደምንሰጥ ሳስበው ይከብደኛል” ብለዋል።
ሌላኛዋ ሴት ተናጋሪ በበኩሏ “ሕዝብ ዳቦ እየጠየቀ ጥይት መመለስ ይገባል ወይ? እኔ ላለፉት 10 ዓመታት ተወክዬ በፓርላማ ሳገለግል ቆይቻለሁ፣ እኔ በፓርላማ ሳለሁ ሕዝቡ ይጠይቅ የነበረውን ጥያቄ ዛሬም ሳይመለስለት ቀርቶ እየጠየቀ ነው። መልስ መስጠት አልቻልንም። መንግስት በየሚዲያው ‘ፀረሰላም ሃይሎች ተመቱ ተገደሉ እያለ ይናገራል’ እኔ ግን ተገድለው ያየሁት ፀረሰላም ሃይሎች ሳይሆኑ ጫማ ጠርገው የሚኖሩ፣ ፑል አጫውተው የሚተዳደሩ ልጆች ናቸው። ሕዝቡ ይህን እያየ እንዴት ብሎ ነው እኛን የሚያምነው? ሕዝቡ መብራት የለውም፣ ውሃ የለውም፣ በሕዝቡ ላይ ከፍተኛ በደል የፈጸምነው እኛ ነን። ይህንንም በይፋ ስንናገር ተልዕኮ አላት እንባለለን። እኔ ምንም ተልዕኮ የለኝም። ያለኝ የማስታወሻ ደብተር ብቻ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።
ግለሰቧ አክለው “የአስቸኳይ አዋጁ የታወጀው ለአንድ ክልል ተብሎ እና የኦሮምያ ክልል ዜጎች ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ተብሎ ነው ወይ? እየተጎዳ እና እየተገደለ ያለው የኦሮሞ ክልል ነዋሪ ነው……እስከመቼ ነው የኦሮሞ ነዋሪዎች ላይ ጥይት የሚርከፈከፈው? ኮማንድ ፖስቱ በኦሮሚያ ክልል ላይ እያዘዘ ግድያዎች እየተፈጸሙ ነው ። እኛ ‘ሕዝቡ ከኛ ጋር ነው’ እንላለን እንጂ ከኛ ጋር አይደለም። ሕዝቡ ዛሬ አንድ መራራ ጉዲናን ለመቀበል ለማየትና ለማጀብ ብሎ በመቶ ሺዎች ወጥቶ መንገድ ዘግቶ ይጨፍራል። እኛን እንደዚህ ሊያየን የሚፈልግ አለን? የለም! በጭራሽ ! ህዝቡ ጠልቶናል!.. ኢህአዴግ አለ ወይ ካላችሁ እዚህ ፓርላማ አደራሽ ተቀምጠን እንደምንለው አይደለም….ኢህአዴግ የለም ብለዋል።” ማለታቸውን ምንጮች ከላኩልን መረጃ ለመረዳት ተችሎአል።
በስብሰባው ላይ ለቀረቡት አስተያየቶችና ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ ሳይሰጥ ስብሰባው ተበትኗል።