የአዲስ አበባ ወጣቶች የአንድነት የቃሊቲ ጉብኝት እንዲካሄድ ጠየቁ

ታህሳስ ፩(አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ወጣቶቹ ለኢሳት በላኩት መልእክት እንደገለጡት በመጪው እሁድ ታህሳስ 7፣ 2005 ዓም አለአግባብ የታሰሩ የሙስሊም ማህበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላትን፣ ጋዜጠኞችንና የተቃዋሚ መሪዎችን በቃሊቲ ተገኝተው ለመጠየቅና ለመዘከር አስበዋል።

ማንኛውም የህገመንግስቱን የእምነት እና ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት መከበር እንዳለበት የሚደግፍ ኢትዮጵያዊ በሙሉ ወደ ቃሊቲ በመሄድ ድጋፉን እንዲያደርግ እንጠይቃለን ያለው መግለጫ፣ እነዚህ ታሳሪዎች ህገመንግስቱ የሰጣቸውን መብት በመጠቀም መላው ህዝባቸውን ሲያገለግሉ የነበሩ የሰላም እና የነጻነት ታጋዮች እንደሆኑ እና ህዝቡም ሰለማዊ አላማቸውን እንደሚደግፍ በእለቱ ማሳየት ይጠበቅበታል ብሎአል።

አልጀዚራ ባለፈው ሳምንት ለጠ/ሚ ሀይለማርያም ደሳለኝ በኢትዮጵያ ውስጥ  ስለታሰሩት የህሊና  እስረኞች  ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩም በእስር ላይ የሚገኙት አሸባሪዎችና ከአሸባሪዎች ጋር ግንኙነት ያላቸው እንጅ የህሊና እስረኞች አይደሉም በማለት መልሰዋል።