የአዲስ አበባ መስተዳድር ለ40 በ60 ቤቶች በድጋሜ ምዝገባ ሊጀምር ነው፤ የምርጫ ቅስቀሳው አካል ነው ተብሎአል

መጋቢት ፳፯ (ሀያ ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የአዲስአበባ ከተማ አስተዳደር በሚያዝያ ወር ለሚያካሂደው የአዲስአበባና የአካባቢ ምርጫ ድጋፍ ለማሰባሰብ
የሚረዳውን የ40 በ60 ቤቶችና የኮንዶምኒየም ቤቶች ዳግም ምዝገባ ለማካሄድ በዝግጅት ላይ መሆኑ ተጠቆመ፡፡
በተወሳሰበ የመልካም አስተዳደር ችግር፣ በሙስናና ብልሹ አሰራር በሕዝብ ዘንድ ክፉኛ የሚወገዘው የኩማ
አስተዳደር በተለይ የአዲስአበባ ከተማ ሕዝብን ቁጣና ኩርፊያ ለማለዘብ ይረዳኛል በሚል ያሰበውን ከቤቶች ልማት
ጋር የተገናኘ ቅስቀሳና የምዝገባ ስራ በሰፊው ለመያዝ በዝግጅት ላይ እንደሚገኝ ምንጮቻችን ጠቁመዋል፡፡

አስተዳደሩ የቤት ፈላጊዎች እና ዳግም ተመዝጋቢዎች መመሪያ ያወጣ ሲሆን በተለይ በ40 በ60 የቤት ልማት
ፕሮጀክት ለመንግስት ሰራተኞች ቅድሚያ ዕድል እሰጣለሁ በሚል በቅርቡ የገባውን ቃል ተከትሎ የመንግስት መ/ቤት
ሰራተኞች በመመሪያው ላይ ውይይት እንዲያካሂዱ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ በውይይቶቹም ኢህአዴግ ልማታዊ መንግስት
መሆኑንና የተጀመረው ልማት ዳር ሊደርስ የሚችለው ሕዝቡ በምርጫ ድጋፉን ሲያሳየው መሆኑን በመጥቀስ ካድሬዎች
በቀጥታና በተዘዋዋሪ ቅስቀሳ በማካሄድ ላይ ይገኛሉ፡፡

በ1996 ዓ.ም የአ/አ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ከ350 ሺ በላይ ነዋሪዎችን ለኮንዶምኒየም ቤቶች የመዘገበ ሲሆን
ከ10 ዓመታት በሃላ የቤት ባለቤት መሆን የቻሉ ዜጎች ቁጥር 80 ሺ ገደማ ብቻ ነው፡፡

ቀሪው ከ270 ሺ በላይ ሕዝብ መንግስት ከአሁን አሁን በዕጣ የቤት ባለቤት ያደርገኛል በሚል በሚጠባበቅበት በዚህ ወቅት “መረጃውን ወቅታዊ ለማድረግና ዕድል ላላገኙት ዕድል ለመስጠት” በሚል ዳግም ምዝገባ ማቀዱ ብዙዎችን ከማሳዘኑም በላይ
በመንግስት ላይ ያላቸው እምነት ሙሉ በሙሉ መሸርሸሩን ያነጋገርናቸው አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል፡፡

ከአስተዳደሩ በተገኘው መረጃ መሰረት 20 በ80 ወይም የኮንዶምኒየም ቤቶች ዳግም ምዝገባ፣40 በ60 በሚባለው
40 በመቶ በመቆጠብ ፣60 በመቶ ከባንክ በሚገኝ ብድር የቤት ባለቤት ለመሆን አዲስ ምዝገባ ፣10 በ90
አነስተኛ አቅም ያላቸው ዜጎች 10 በመቶ ቆጥበው 90 በመቶ ከባንክ በመበደር የስቱዲዮ ቤቶችን ለመገንባት
የሚያስችል አዲስ ምዝገባ በሚያዝያ ወር 2005 ዓ.ም ይጀመራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በጉዳዩ ላይ አስተያየት የተጠየቁ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አባል በሰጡት አስተያየት ኢህአዴግ ብቻውን
በሚወዳደርበት ምርጫም ላይ ቢሆን ሕዝቡን መፍራቱ ምን ያህል ከህዝብ መነጠሉን እንደሚያሳይ ጠቁመው የቤት ምዝገባ
ማባባያዎቹ ለጊዜው ሊረዱት ቢችሉም በዘላቂነት ግን የሚረዱት አይሆኑም ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት እነኦማር ሐሰን
አልበሽርን የመሳሰሉ አምባገነን መሪዎች የፖለቲካ እስረኞችን ለመፍታት በተገደዱበት ወቅት ኢህአዴግ በሕግ ጥላ
ስር ያሉትን የፖለቲካ እስረኞች ሳይቀር ማሰቃየትና ሰብዓዊ መብት መግፈፍ እንደስራ መያዙ ይበልጥ ከሕዝብ ጋር
እያራራቀው እንደሚገኝ በምሳሌነት አንስተዋል፡፡

አክለውም ኢህአዴግ በቤት ልማት ሰበብ በመንግስት ሐብትና ንብረት እየተጠቀመ የምርጫ ቅስቀሳ ማከናወን ሕገወጥ
መሆኑን እንኳን አለማስተዋሉ የሚያሳዝን ነው ብለዋል፡፡

በዘንድሮው የአዲስ አበባማ የክልል ምርጫ 33  የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደማይሰታፉ መግለጻቸው ይታወቃል።