የአባይ ግድብ ግንባታ ጉዳይ ላይ የተደረገው ስምምነት ችግር እየገጠመው መሆኑን ግብጽ አስታወቀች

(ኢሳት ዜና–መስከረም 26/2010) ኢትዮጵያ በጀመረችው የአባይ ግድብ ግንባታ ጉዳይ ላይ የተደረገው ስምምነት ችግር እየገጠመው መሆኑን ግብጽ አስታወቀች።

ግብጽ እንደምትለው የአባይ ግድብን በተመለከተ ከሱዳንና ከኢትዮጵያ ጋር የተካሄደው የሶስትዮሽ ስምምነት በአንዳንድ ምክንያቶች እየተስተጓጎለ ይገኛል።

ጉዳዩን ይፋ ያደረጉት የግብጽ ውጭ ጉዳይ ሚኒስተር አጋጠሙ ስላሏቸው ችግሮች ዝርዝር ማብራሪያ ከመስጠት ግን ተቆጥበዋል።

የግብጽ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሹኩሪ የሶስትዮሽ ስምምነቱን አደጋ ላይ የሚጥል እንቅፋት ማጋጠሙን ይናገራሉ።

ይህ የሶስትዮሽ ስምምነት የአባይ ግድብን በተመለከተ በኢትዮጵያ፣ሱዳንና ግብጽ መካከል የተፈጸመ ነው።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጣር በ2015 መጋቢት ወር ላይ የተፈረመው የሶስትዮሽ ስምምነት ኢትዮጵያ የአባይ ግድብን ሳትገነባ የተፋሰሱን ሀገራት በተለይም ግብጽን በማይጎዳ ሁኔታ ማከናወን አለበት።

ይህም በጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ፊርማ የተረጋገጠ መሆኑን የግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገልጸዋል።

ግብጽ በበኩሏ የአባይ ግድብ መገንባትን እንደማትቃወምና የኢትዮጵያን የልማት ፍላጎት እንደምትቀበል ፈርማለች።

ሱዳን ደግሞ በዚህ ስምምነት ሶስተኛ አካል ሆና ጉዳዩን በአወንታዊነት መቀበሉ ነው የሚነገረው።

ይህ ስምምነት በአንዳቸው አካል ቢጣስ ወይም ችግር ቢገጥመው ገለልተኛ በሆነ አካል ጉዳዩ እንደሚታይና ግጭት እንዳይፈጠር ሳይንሳዊና ቴክኒካል በሆነ መንገድ ችግሩን እንደሚፈታም ሶስቱም ሀገራት ተስማምተዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ዝርዝር ምክንያቱን ባልጠቀሱበት ሁኔታ የግብጽ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሹኩሪ ሂደቱ እየተጓተተና ችግር እንደገጠመው ለሀገራቸው መንግስታዊ ጋዜጣ አልሃለም ይፋ አድርገዋል።

ይህም በቴክኒካል መንገድም ሆነ በፖለቲካዊ መፍትሄ ሊፈታ የማይችል ችግር መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ለጋዜጣው ገልጸዋል።

እንደ ግብጹ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገለጻ ስምምነቱን የፈረሙት ሶስቱ ሀገራት የቴክኒክ ሪፖርቱ ከመውጣቱ በፊት የግድቡ ግንባታ ማለቅ እንደሌለበት በመተማመናቸው ጉዳዩን እንዲያጤኑት ጠይቀዋል።

ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ እየገፋችበት በመሆኑም ጉዳዩ ያሳስበናል ብለዋል።

ኢትዮጵያ የጀመረችውን የአባይ ግድብ በመግፋት የውሃ መሙላት ስራው እንደሚቀጥል እየገለጸች ትገኛለች።

ኢትዮጵያ ግድቡን አጠናክራ እንዳትገፋ እያደረጋት ያለው የገንዘብ እጥረት መሆኑ ይነገራል። በቅርቡም ከገንዘብ እጥረት ጋር በተያያዘ በርካታ ሰራተኞች መቀነሳቸውን መዘገባችን ይታወሳል።