የታዋቂው ፖለቲከኛ እና ጸሀፊ አስገደ ገብረስላሴ ልጅ ታፍኖ መወሰዱ ታወቀ

ሚያዚያ ፳፩ (ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የህዝባዊ ወያን ሀርነት ትግራይ ነባር አባል፣ በአሁኑ ጊዜ የአረና ትግራይ ከፍተኛ የአመራር አባል እና ጸሀፊ የአቶ አስገደ ገብረስላሴ ልጅ የሆነው  አክህፎም አስገደ የታሰረው ባለፈው አርብ ነው።

ሚያዚያ 16 ቀን 2005 ዓም ቀዳማዊ ወያኔ ፖሊስ ጣቢያ ተብሎ በሚጠራ እስር ቤት መታሰሩን  እሁድ ሚያዚያ 20  ደግሞ በመቀሌ ውስጥ በሚገኝ ህጋዊ እውቅና በሌለው ድብቅ እስር ቤት ውስጥ መታሰሩን ወላጅ አባቱ አቶ አስገደ ገብረስላሴ ለኢሳት ገልጸዋል። በመቀሌ ህጋዊ የሆኑ 7 ፖሊስ ጣቢያዎች ብቻ መኖራቸውን የገለጹት አቶ አስገደ፣ ልጃቸው የታሰረበት ቦታ  በክልሉ ፖሊስ ኮሚሺነር አማኑኤል ለገሰ ብቻ የሚመራ ድብቅ እስር ቤት መሆኑን ገልጸዋል

ዜሮ ስድስት እየተባለ የሚጠራው እስር ቤት ከ1968 ዓም ጀምሮ የተቋቋመ የህወሀት እስር ቤት ነው። ህወሀት ስልጣን ከያዘ በሁዋላም ይህን እስር ቤት አለዘጋውም።

የ26 አመቱ ወጣት አክህፎም አስገደ ከአራት ወራት በፊት ለ5 ቀን ታስሮ ከፍተኛ ድበደባ ደርሶበት እንደነበር አባቱ ተናግረው የክልሉ ፖሊስ አዛዥን ልጃቸውን እንዲፈታላቸው ዛሬ ጠይቀው እንደነበር አቶ አስገደ ተናግረዋል።

አቶ አስገደ የህወሀት/ኢህአዴግን  አገዛዝ በመተቸት ይታወቃሉ። ገሀዲ በሚለው መጽሀፋቸው ሟቹ አቶ መለስ ዜናዊን ጨምሮ ከፍተኛ የህወሀት ባለስልጣናት በአገሪቱ ላይ የሰሩትን በደል ዘርዝረው አቅርበዋል። በተለያዩ ድረገጾች ላይ የሚያወጡዋቸው ጽሁፎች የገዢውን ፓርቲ ሰዎች ሲያስቆጡ መቆየታቸው ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ህገመንግስት ዜጎች በታሰሩ በ48 ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ከቤተሰቦቻቸው እና ከጠበቆቻቸው ጋር እንዲገናኙ ያዛል። አቶ አስገደ በጣም የሚወዱትን ልጃቸውን ማሰራቸውና ማሰቃየታቸው እርሳቸውን ለመበቀል በማሰብ የተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

በቅርቡ የአቶ አባይ ወልዱን አገዛዝ በመተቸት ያቀረቡትን ጽሁፍ በረቡእ የድረገጽ ዳሰሳ ዝግጅት ላይ መከተታል ተችላላችሁ።