የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎችና ታዋቂ ሰዎች የግንቦት 20ን በአልን በተመለከተ አስተያየቶችን ሰጡ

ግንቦት ፳(ሃያ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኦሮሞ ነጻነት ግንባር የአንደኛው ክፍል ሊቀመንበር የሆኑት ጄል ከማል ገልቹ እንደተናገሩት የግንቦት20 በአል የኢትዮጵያ ህዝብ ከአንድ አስከፊና አንባገነን ስርአት ወደ አስከፊ፣ አንባገነንና ዘረኛ ስርአት የተሸጋገረበት ነው ብለዋል።

ግንቦት20 ከኢትዮጵያ ታሪክ፣ ልምድና ምኞት አብሮ የማይሄድ ዘረኛ መንግስት ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈጠረበት አሳዛኝ ቀን ነው ሲሉ አክለዋል

የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዚዳንትና የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ሊ/መንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንደተናገሩት ደግሞ ግንቦት 20 የደርግ አሰቃቂ ስርአት ወድቆ ዲሞክራሲያዊ ህዝባዊ መብት የተከበረባት፣ አንድነቷንና ሉአላዊነቱዋን የበለጸገች አገር እንዲመሰረት ሙከራውየተጀመረበት ቀን ነው ያሉት ዶ/ር ነጋሶ፣ ህገመንግስት የተረቀቀ ቢሆንም ፣በ23 አመት ውስጥ ብዙ ተጀምረው ወደ ሁዋላ የተመለሱና ያልተሰሩ ስራዎች መኖራቸውን ተናግረዋል።

ህገመንግስት መረቀቁንና ብሄሮች ራሳቸውን ማስተዳደር መጀመራቸው እንዲሁም የኢኮኖሚ እድገት እንደ ትልቅ ነገር የሚታይ ቢሆንም፣ አንዳንድ ጉዳዮች ላይ አሁንም ያልተሟሉ ነገሮች አሉ ብለዋል

ኢህአዴግ መራሹ ሃይል ደርግን በመደምሰስ የህግ የበላይነትና ዲሞክራሲን አሰፍናለሁ ብሎ ህገመንግስት ቢያረቅም፣ ኢህአዴግ በወረቀት የሰፈረውን ለመተርጎም ከደርግ የማይተነሳስ አፈናና ጭኮናና መፈጸሙን የገለጹት ደግሞ ታዋቂው ፖለቲከኛና የህወሃት ታጋይ የነበሩት አቶ አስገደ ገብረስላሴ ሲሆኑ፣ ከጥይት ጩኸት አለመላቀቃችንን፣ ሰብአዊ መብቶች አለመከበራቸውን ገልጸዋል።

ከፊውዳሊዝም አስተዳዳር በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ በመሬት ጉዳይ ላይ ጭሰኛ መሆኑን የገለጹት አቶ አስገደ በአገሪቱ ውስጥ ያለውን አፈና ዘርዝረው አቅርበዋል

ከፖለቲካ ድርጅት መሪዎች ጋር የተደረገው ሙሉ ቃለምልልስ በሌላ ዝግጅት ላይ እንደሚቀርብ ለመግለጽ እንወዳለን።