የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ በጭቅጭቅና በንትርክ እየተካሄደ ነው

(ኢሳት ዲሲ–የካቲት 8/2010)

የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ከ3 በተከፈለ ቡድን በጭቅጭቅና በንትርክ እየተካሄደ መሆኑን የኢሳት ምንጮች ገለጹ።

ፋይል

ስብሰባው በዘለፋና በስድብ ታጅቦ በወልቃይት ኮሚቴ አባላት አያያዝ፥ በመከላከያና ደህንነት ጣልቃ ገብነት እንዲሁም በሕወሃት የበላይነት ጉዳይ ላይ ክርክር ተደርጎ አሁን ባለው ሁኔታ ወደ ግለ ሂስ ተገብቷል።

በአቶ ገዱ አንዳርጋቸው የሚመራው ቡድን ችግራችን ውጫዊና በክልላችን የሚደረግ ጣልቃገብነት ነው እያለ ነው።

በእነ አቶ አለምነው የሚመራው ቡድን ደግሞ የራሳችንን ችግር በውጭ ማሳበብ አይገባም፥ ከመከላከያና ከሕወሃት የሚደርግልን ድጋፍም ጠቅሞናል ሲሉ ተከራክሯል።

በብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ የኮ/ል ደመቀ ዘውዱ ፥ የመከላከያ ጣልቃገብነትና የህወሃት ጉዳይ አጀንዳ ነበሩ ፡፡

የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ከጀመረ ከ12 ቀን በላይ ሆኖታል።

ይህ ስብሰባ ቀደም ሲል ጥር 9 /2010 ተጀምሮ በክልሉ በሚገኙ አብዛኛው ከተሞች ሕዝባዊ አመፅ በመቀስቀሱ እና ተቃውሞው በማየሉ ጥር 13 / 2010 ተቋርጦ ነበር።

ስብሰባው በድምሩ 15 ቀን ፈጅቶም ቢሆን አሁንም መቋጫ አላገኘም ፡፡

በዚህ ስብሰባ የእነ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ቡድን በአንድ ወገን እንዲሁም የእነ አቶ አለምነው መኮነን  ቡድን በሌላ ወገን በሦስተኛው ረድፍ ደግሞ ከሁለቱም ቡድኖች ውጭ የቆሙ እንዳሉ የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

በዚሁም መሰረት በእነ አቶ ገዱ ቡድን አቶ ተስፋዬ ጌታቸው፣ ዶ/ር አምባቸውና እነ ብናልፍ አንዷለም እንዳሉበት ሲነገር በእነ አቶ አለምነው መኮነን ቡድን ደግሞ አቶ ከበደ ጫኔ ፣ አቶ ምግባሩ ከበደና  አቶ አህመድ አብተው እንዳሉበት መረጃዎች ያሳያሉ።

በእነ አቶ በረከት ስምኦን፣ በአቶ አዲሱ ለገሰና በአቶ ህላዊ ዬሴፍ ይደገፋል ከሚባለው የአቶ አለምነው ቡድን በተጨማሪ ከሁለቱ ውጭ የቆሙት እነ ደመቀ መኮንን ናቸው።

በእነ አቶ ገዱ በኩል የህወሃት ጣልቃ ገብነት፣ በተለይ በክልሉ ያለውን አለመረጋጋት እንዲፈጠር ዋናው ምክንያት የወልቃይት ሕዝብ ኮሚቴ አባላት የተያዙበት መንገድ አግባብ አይደለም የሚል ይገኝበታል።

በየጊዜው ከፌደራል በሚመጡ የፀጥታ ሰዎች ከክልሉ እውቅና ውጭ እየተያዙ መወሰድ እንዲሁም መገደል  የትግራይ ክልል እና የፌዴራል መንግስት ልዩነቱ አለመታወቁ፣  በተለይ በክልሉ  የተለዩ ሃሳቦችን ማንሳት “የአርበኞች ግንቦት 7” አባል ነህ በማለት ያስፈርጃል ሲሉም ተከራክረዋል።

የክልሉ አመራሮች በስብሰባ ወቅት የምንወያይባቸው ጉዳዮች፣የምንወስናቸው ጉዳዩች በፍጥነት ለህወሓት ሰዎች ይደርሳቸዋል፣ እነሱም ያለምንም እፍረት በቀጥታ ስልክ በመደወል ዛሬ እንደዚህ ዓይነት ውሳኔዎች ማስተላለፋችሁ ትክክል አይደለም እንባላለን፣ ከዚህ አልፎም ዛቻ ሁሉ አለብን ሲሉም እውነታውን አፍረጥርጠዋል።

ከኦሮሚያ ክልል ጋር ያደረግነው ግንኙነት፣የአርቲስት ቴዎድሮስ ኮንሰርት፣ የአማራ መገናኛ ቡዙሃን የሚሰራቸው ፕሮግራሞች በሙሉ እንደ ወንጀል እየቀረቡ እኛን ማሸማቀቅ ተገቢ አይደለምም ነው ያሉት።

በተለይም የፌዴራል መንግስት ተቋማት የሆኑ የመከላከያ እና የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ተቋማት ሰፊ ጣልቃ ገብነት በአማራ ክልል አለመረጋጋትን ፈጥሮ ይገኛልም ብለዋል።

በተጨማሪም የፌደራል አመራሮችና በተለይም እነ በረከት ቀጥተኛ በሆነ ጣልቃ ገብነት በስራችን ላይ እንቅፋት ፈጣሪዎች ሆናችኋል ሲሉም ነው የተናገሩት።

የእነ አለምነው መኮንን ቡድን ግን የወልቃይት ጉዳይ ከዚህ ደረጃ እንዲደርስ ያደረጋቹሁት እናንተ ናችሁ ፣ ውስጣዊ ችግሮችን ወደ ውጭ እየገፋችሁ የህወሃት ጣልቃ ገብነት የበላይነት አለ ማለት እንዲሁም ሰላምና ፀጥታ የሚያስከብሩ የፌዴራል ተቋማትን ከአጋርነት ይልቅ በጠላትነት መፈረጃቹሁ ተገቢ አይደለም ሲሉም ተቃውመዋል፡፡

ነባር አመራሮች የሚሰጡትን ድጋፍ እንደ ጣልቃ መግባት መመልከት ስህተት ነው ባይ ናቸው።

የኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ጉዳዩ በክልሉ ይታይ ብሎ መከራከርዥ፥ በሽብር ስራ የሚያዙ ሰዎችን መያዝ ስህተት ነው ማለት ምን ማለት ነው ፣በተለይም ችግሩ የኛ ሆኖ እያለ ወደ ውጭ ማየት ተገቢ አይደለም ሲሉም የእነ አቶ ገዱን ቡድን ተቃውመዋል፡፡

በዚህ ሁኔታም ጭቅጭቁ እና ንትርኩ እንዲሁም ሂስና ግለሂሱ ተቀበል አልቀበልም በሚል እሰጣ ገባ የብአዴን ማዕከላዊ አባላት መሰዳደባቸው ተነግሯል።

አለምነው መኮነን ለገዱ አንዳርጋቸው “አንተም ሆንክ እኔ በክልሉ አመራርነት አንቀጥልም” ብለው መናገራቸውም በተሰብሳቢዎቹ ላይ አግራሞትን አስከትሏል።

ምክንያቱም ስብሰባው ለይስሙላ የሚደረግ እንጅ ቀድሞ ያለቀና የተወሰነ ነገር እንደሆነ ምልክት ያሳየ ስለነበር ነው ተብሏል።

በዚህ ስብሰባ ላይ የማይመለከታቸው የደህንነትና የመከላከያ ሰዎችም ገብተዋል እንዲሁም በነባር ታጋይ ስምም የእነ አቶ አዲሱ ለገሰ ሰዎች በስብሰባው ላይ መገኘታቸው ተነግሯል።

ይቅርታ እንጠይቅ አንጠይቅ ጥፋተኛ ነን አይደለም የንትርክ አጀንዳ መሆኑም ነው የተገለጸው፡፡

ስብሰባው ሲጠናቀቅ ታይቶ የማይታወቅ ውሳኔ ይተላለፋል ተብሎ እንደሚጠበቅና የሚታገዱ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትም እንደሚኖሩ የብአዴን ጽሕፈት ቤት አስታውቋል።