የቅድመ ውህደት ስምምነቱ የቅንጅትን ህዝባዊ መንፈስ ይመልሳል ሲል አንድነት አስታወቀ

ሰኔ ፮(ስድስት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ፓርቲው ” ውህደታችንን በማጠናከር  የቅንጅትን ህዝባዊ መንፈስ ዳግም እንመልሳለን በሚል ርእስ ባወጣው መግለጫ ሁለቱ ፓርቲዎች “ከጥልቅ ውይይት በኋላ ወቅታዊው የፖለቲካ ሁኔታ የሚፈልገውን በመገንዘብ፤ የህዝቡን ጥያቄ መመለስ የሚችል የተባበረ የፖለቲካ ሃይል ለመፍጠርና የቅንጅትን ህዝባዊ መንፈስ ለመመለስ የሚያስችላቸው ደረጃ ላይ ” ደርሰዋል ብሎአል።

ሁለቱ ፓርቲዎች ሰኔ 1 ቀን ለበርካታ ወራት በጋራ ሲሰሩበት የነበረውን የውህደት ስምምነት ከጫፍ በማድረስ የቅድመ ውህደት ስምምነት መፈረማቸውን ያወሳው ፓርቲው፣  ህዝቡ በስምምነቱ ቢደሰትም  የስርአቱ ደጋፊዎች ውህደቱ እንዳይሳካ ሙከራ አድረገው እንደከሸፈባቸው አትቷል።

ፓርቲው ውህደቱን ለመፈጸም ቀሪ ስራዎች እንዳሉ ቢገልጽም፣ ውህደቱ ተፈጻሚ እንደሚሆን ያለውን እምነት ገልጿል። ሌሎች ፓርቲዎችም ተመሳሳይ ውህደት በመፈጸም የቅንጅትን መንፈስ እንዲያድሱ ጥሪ አቅርቧል።