የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በገንዘብ የአለማችን ሀብታም ጠቅላይ ሚኒስትር ለመሆን የበቁ መሆናቸው ተዘገበ

ግንቦት  ፲፱(ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- “ዘ ሪቸስት ዳት ኦርግ” የተሰኘው ድረ-ገፅ ይፋ እንዳደረገው፤ የቀድሞው ጠ/ ሚ/ር መለስ ዜናዊ የ3 ቢሊዮን ዶላር ባለቤት በመሆን ነው ከዓለማችን ፖለቲከኞች የሁለተኛ ደረጃን የያዙት።

“ዘ ሪቸስት” የተሰኘው ይህ ድረ-ገፅ፤ በአንደኛ ደረጃ ባለፀጋ ሲል ያሰፈራቸው የቀድሞውን የጣሊያን ጠ/ሚ/ር ሲልቪዮ በርሎስኮኒን ሲሆን አንደኛ ደረጃ ያስቀመጣቸውን የ5.9 ቢሊዮን ዶላር ያፈሩት ከፖለቲካው መድረክ ሳይሆን በሜዲያው መስክ ከተሰማሩበት ሥራ ነው።

የጣሊያኑ ሴሪአ የእግር ኳስ ክለብ የሆነው የኤ.ሲ. ሚላንና  የቴሌሚላኖ የቴሌቪዥን ጣቢያ ባለቤት የቀድሞው የጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር ሲልቪዮ በርሎስኮኒ አሁንም የተንደላቀቀ ሕይወትን በመምራትና ዳንኪራ በመጨፈር የጣሊያንን ሜዲያዎች የፊት ገፅ የያዘ ፣ ርዕሰ-ዜና የሚሰራላቸው ታላቅ ሰው ናቸው ብሏቸዋል – ዘ ሪቸስት ዳት ኦርድ።

ከፍተኛ የገዘብ ምንጫቸው እንደሆነ የሚነገርለትና ላለፉት 25 ዓመታት በባለቤትነት የያዙት የአውሮፓው ታዋቂ የግር ኳስ ክለብ ኤሲ ሚላን ሲሆን፤ የ76 ዓመቱ በርሎስኮኒ በኢጣሊያ ቁጥር አንድ የሆነ የኢንተርቴይንመንት እንዲሁም የኢንሹራንስ፣ የባንክና የፊልም ፕሮዳክሽን ኩባንያዎች ባለቤት ጭምር ናቸው።

በግላቸው ከነዚህ ዓይነት የንግድ ዘርፎች ጭራሽ የሌሉበት የቀድሞው ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ ከሊባኖሱ ጠ/ሚኒስትርና የንግድ ሰው ነጀብ ሚካቲ የ3 ቢሊዮን ዶላር ባለቤት በመሆን የዓለማችን ሁለተኛ ባለፀጋ ፖለቲከኛ የተሰኙ ሲሆን የሀብት ምንጫቸው ፖለቲካ የተባለላቸው ሆነዋል።

በ3 ቢሊዮን ዶላር ጎን ለጎን ሆነው የተቀመጡት የቀድሞው ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊንና የሊባኖሱን ጠ/ሚ/ር ነጂብ ሚካቲ የሚለያቸው የሀብት ምንጫቸው በአፍሪካ ያንሰራፉትና ያስፋፉት የቴሌኮም ኩባንያና ሌሎች የንግድ ሥራዎቻቸው ሲሆን የአቶ መለስ ዜናዊ ግን ፖለቲካ ብቻ መሆኑ ነው።

በዚህ የሀብታሞች ተርታ ሦስተኛ የተቀመጡት የሊባኖስ ጠ/ሚ/ር ሳድ አድን ራፊቅ አል ሐሪሪ ሲሆን የሀብት ልካቸውም 1.9 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ነው።

ታዋቂ የንግድ ሰው፣ ባለኩባንያና ፖለቲከኛው ራፊቅ አል ሐሪሪ የሃብት ምንጮቻቸውንም ቢዝነስ ነው ተብሏል በ ዘ ሪቸስት ዳት ኦርግ ዘገባ።

ከሴት ጠ/ሚ/ሮች የፓኪስታኗ ቤናዚር ቡቶ የ850 ሚሊዮን ዶላር ባለቤት ሆነው ከሴት ፖለቲከኞች በብቸኝነት ተጠቅሰዋል።

ያአቶ መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ባለቤታቸው በ6000 ብር ደመወዝ ሲተዳደሩ ቆይተው በድህነት ኖረው በድህነት የሞቱ መሆኑን በመግለፅ ሲከራከሩላቸው፣ እንዲያውም የዓለማችን ደሃና ጠንካራ መሪ ተብለው ሊፃፍላቸው ይገባል በማለት ሲከራከሩ እንደነበር ይታወሳል።