የስፔይ ኩባንያ በኢትዮጵያ የቆላ ዝምብ በሽታን ለመከላከል ሰው አልባ አውሮፕላን ሊጠቀም ነው

ኢሳት (መጋቢት 22 ፥ 2008)

አንድ የስፔን ኩባንያ ሰው አልባ አውሮፕላኖች በመጠቀም በቆላ ዝንቦች አማካኝነት የሚመጣውን የእንቅልፍ በሽታ በማይራቡ የቆላ ዝምቦች ለመከላከል እንደሚቻል ገለጸ።

የእንስሳት ደም የሚመገበው የቆላ ዝምብ፣ በሰዎች ላይ የድካምና ትኩሳት መለያ ባህርይ ያለው የእንቅልፍ በሽታ እንደሚያመጣና፣ በጊዜው ህክምና ካላገኘ በሰውና በእንስሳት ላይ ሞት ሊያስከትል እንደሚችል ተነግሯል።

ኢትዮጵያን ጨምሮ ከሰሃራ በታች ባሉት አገራት በብዛት የሚገኘው የቆላ ዝምብ፣ በየአመቱ ከ100ሺ ሰዎች በላይ በበሽታው እንደሚያዙ ጥናቶች ያመለክታሉ። የቆላ ዝምብ ንክሻ፣ እንስሳትን ሽባ ሊያደርግ እንደሚችል ተመራማሪዎች ይገልጻሉ።

በስፔይን  አገር የሚገኘው ድርጅት “ሰው አልባ አውሮፕላኖች የቆላ ዝምብ ለመቆጣጠር” በሚል ፕሮጄክት በሰው አልባ አውሮፕላኖች አማካኝነት ወንድ የቆላ ዝንብ ነፍሳትን በጨረር በማምከን በኢትዮጵያ ውስጥ ተሰራጭቶ የሚገኘውን በሽታ እንደሚቆጣጠረው ገልጿል።

ድርጅቱ እንዳለው በኢትዮጵያ ውስጥ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ወንድ የወባ ትንኞች ላይ የተደረገው ተሞክሮ አመርቂ ውጤት ስላስገኘ፣ የቆላ ዝምብ ሙካራውም ከዚህ ልምድ የተወሰደ ተሞክሮ እንደሆነ ገልጿል።

ትናንሽ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን በመጠቀም መቶሺ ወንድ የቆላ ዝምቦችን በጫካ ውስጥ ለማሰራጨት የታሰበ ሲሆን፣ የመከኑት ወንድ የቆላ ዝምቦች በአካባቢው ሊራቡ ከሚችሉ ሴት የቆላ ዝምቦች ጋር ግንኙነት ሲፈጥሩ እንደሚሞቱ ለማወቅ ተችሏል።

በሰው ከሚበሩ አውሮፕላኖች ይልቅ ሰው አልባ አውሮፕላኖች የተመረጡበት ምክንያት፣ ረጅም ሰዓት መብረርና፣ በብዙ ቦታ ላይ የቆላ ዝምቦችን ማሰራጨት በመቻላቸው ነው ተብሏል። ሰው አልባ አውሮፕላኖችም ከመሬት በቅርብ እርቀት መብረር የሚችሉ በመሆናቸውና የቆላ ዝምቦችን ያለጉዳት ማሰራጨት መቻላቸውን ተነግሯል።

አንድ ሰው አልባ አውሮፕላን 5ሺ የቆላ ዝምቦችን 40 ስኩዌር ማይል (104 ስኩዌር ኪሎሜር) በሽታው በብዛት በሚገኝበት አካባቢ ማሰራጨት እንደሚችል ተነግሯል።