የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ጎንደር ላይ ታሰሩ

ጥር ፳፪ (ሃያ ሁለት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከድንበር ጋር በተያያዘ በኢትዮጵያ እና በሱዳን መንግስታት መካከል ያለው ንግግር ለህዝብ ግልጽ እንዲሆን ለመጠየቅ በመጪው እሁድ በጎንደር ከተማ ለማካሄድ የታቀደውን ሰልፍ ለማስተባበር ወደ ጎንደር ያቀኑት የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ፣ ሌሊት ከተማዋ ደርሰው በማግስቱ የቅስቀሳ ስራ ሲጀምሩ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል።

አመራሮቹ ሲታሰሩ የተመለከተ አንድ ታዛቢ ከኢሳት ጋር ባደረገው አጭር ቆይታ እንደገለጸው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊው ወጣት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣   ዮናታን ተስፋየ፣ ወይንሸት ሞላ፣ አቤል ኤፍሬምና ጌታነህ ባልቻ ታስረዋል።

ሰማያዊ ፓርቲ በመጪው እሁድ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ የቅስቀሳ ስራ በመስራት ላይ ይገኛል። ሰሜን ጎንደር ፖሊስ አዛዥን ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።

ባለፈው አርብ በትግራይ አዲግራት ከተማ ከህዝብ ጋር ለመወያየት ለቅስቀሳ ስራ ሄደው የነበሩት አቶ አስገደ ገብረስላሴ፣ መምህር አብርሃ ደስታና አቶ አምዶም ገብረስላሴ መደብደባቸው ይታወቃል።