የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር የአውሮፓ ህብረት በኢትዮጵያ ላይ ጠንካራ አቋም እንዲይዝ ጠየቁ

ነሃሴ ፮(ስድስት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢ/ር ይልቃል ከ20 የአውሮፓ ህብረት አገራት ልኡካን ጋር በህብረቱ ጽ/ቤት ተገኝተው በተወያዩበት ወቅት እንደገለጹት ፣ኢትዮጵያ አሁን

ካለችበት ችግር ወደ ባሰ ችግር ሳትገባ ህብረቱ አፋጣኝ እርምጃ ሊወስድ ይገባዋል።

ኢ/ር ይልቃል ገዢው ፓርቲ ስለሚያደርገው አፈና፣ በሚዲያው ላይ ስለሚወሰደው እርምጃ፣ በእስር ላይ ስለሚገኙት ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞችና ጸሃፊዎች የተናገሩ ሲሆን፣ ኢህአዴግ

በርእዮታለም መደናበርና በአመራር ብቃት ማነስ መቸገሩን በመግለጽ መጪውን ምርጫ እንደማያሸንፍ በማወቁ ከወዲሁ የአፈና ስልቱን ተግባራዊ እያደረገ ነው ሲሉ አክለዋል።

ኢ/ር ይልቃል ኢህአዴግ እየተከተለ ያለው መንገድ እና አውሮፓኖች የያዙት አቋም ኢትዮጵያን የሚጎዳ መሆኑን በአጽንኦት ተናግረዋል። ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞችና ጸሃፊዎች ሲታሰሩ

ህብረቱ እርምጃ አለመውሰዱን የገለጹት ኢ/ር ይልቃል፣ የህብረቱ አባላት በሙጋቤ ላይ ከወሰዱዋቸው እርምጃዎች መካከል ትንሹን እንኳ በኢህአዴግ ላይ ቢወስዱ ለውጥ ማምጣት

እንደሚቻል አስረድተዋል። አውሮፓኖች ለራሳቸው ሲሉ በኢትዮጵያ ላይ አንድ እርምጃ መውሰድ እንዳለባቸው ኢ/ር ይልቃል አሳስበዋል።