የህወሀት መስራችና የቀድሞ ሊቀ-መንበር  የአቶ ስብሀት ነጋ ልጅ፤ ጎተራን  ለአምሰት አመት ኮንትራት በ600 ሺህ ብር እንደወሰደው ፎርቹን ሳምንታዊ ጋዜጣ ዘገበ።

ታኀሳስ ፳፰(ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-እንደ ጋዜጣው ዘገባ የአክሊል ክሬቲቭ ኤጄንሲ ባለቤት የሆነው ተከስተ ስብሀት  ነጋ፤ በአካባቢው ያለን 4000 ስኩዌር ኪሎ ሜትር መሬትን ለተለያዩ መዝናኛዎች፣እንዲሁም  43 ትልልቅ ጎተራዎችን ለማስታወቂያ ስራ  ነው በ600 ሺህ ብር ለአምስት ዓመት ኮንትራት የወሰደው።

ለጥቂት ቀናት የሚለጠፍ አንድ ማስታወቂያ ብቻ ብዙ ሺህ ብር  በሚያስከፍልበት በአሁኑ ወቅት፤ ትልቅ አደባባይ የሆነውን የጎተራን አካባቢና ትላልቆቹን  43 ጎተራዎች በአንድ ዓመት በመቶ ሀያ ሺህ ብር ሂሳብ  ለአቶ ስብሀት ነጋ ልጅ መሰጠታቸው፤ ስርዓቱ  የተዘፈቀበትን  የሙስና ጥልቀት የሚያሳይ ነው ሲሉ የጋዜጣውን ዘገባ ያነበቡ ሰዎች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። ጋዜጣው በሌላ ዘገባው የሕወኃት ንብረት የሆኑትን ኤፈርትን እና መስፍን ኢንጂነሪንግን  ሲያስተዳድር የቆየው የቀድሞው  የአዲስ አበባ ከንቲባ የኣርከበ ዕቑባይ ወንድም  ጌታቸው ዕቑባይ በዚህ ሳምንት  የኢትዮጰያ የመንገዶች ባለስልጣንን በሀላፊነት እንደሚረከብ አስነብቧል።