የሃገር ውስጥ የደህንነት መምሪያ ሃላፊው አቶ ወልደስላሴ ወልደሚካኤል በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ዋሉ፤

ነሃሴ ፳፬(ሃያ አራት)ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ፋና እንደዘገበው ፤ግለሰቡ በቁጥጥር ስር የዋሉት የነበራቸውን ስልጣን ያለአግባብ በመጠቀም ምንጩ ያልታወቀ ሃብት በማፍራት የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል በሚል  ተጠርጥረው ነው ።

ፋና ይህም ቢልም አቶ ወልደስላሴ ከደህንነት ዋና ሹሙ ከአቶ ጌታቸው አሰፋ ጋር ጠብ ውስጥ ገብተው መቆየታቸው በስፋት ሲነገር ቆይቷል።

በተለይ መቀሌ በተካሄደው የህወሀት ጉባኤ ላይ በአቶ ጌታቸው አሰፋ እና በአቶ ወልደስላሴ መካከል ከፍተኛ ጭቅጭቅ ተፈጥሮ የነበረ ሲሆን፤በጉባኤው አቶ ወልደስላሴአቶ ጌታቸው አሰፋን  “የ አል አሙዲ ተላላኪ ሆኗል” እስከማለት ድረስ ዘልፈዋቸው  ነበር።

በዚህም ሳቢያ የደህንነት ሹሙ አቶ ጌታቸው ቂም በመያዝና ከወራት በፊት በተደረገ ግምገማ አቶ ጌታቸውን ከሙስና ጋር በማያያዝ ከሀላፊነታቸው እንዲወገዱ አስደርገዋቸዋል።

ከወራት በፊት በዚህ መልኩ ከሀላፊነታቸው የተወገዱት አቶ ወልደሥላሴ ዛሬ በሙስና ክስ በቁጥጥር ስር ውለዋል።

ከፌደራል ስነምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው  ፥ ተጠርጣሪው በፌደራል ከፍተኛ ፍርድቤት ቀርበው የ14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል።

የዛሬ አመት ገደማ ኮሚሽኑ በአቶ ወልደስላሴ  ወንበር ላይ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩትን አቶ አይቼው ተፈታን በተመሳሳይ ወንጀል ከሷቸው በአሁን ጊዜ  ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ እንደሆነም ፋና ጨምሮ ዘግቧል  ።

አቶ ወልደስላሴ የህወሀት አባልና የትግራይ ልማት ማህበር የቦርድ አባል ናቸው።

ጸረ-ሙስና ኮሚሽን የውስጥ ተቀናቃኞችንና አፈንጋጮችን ማጥቂያ  እንደሆነ ይታመናል።