ውሃ ፣መብራት፣ቴሌ አሁንም ሕዝቡን እያስመረሩት ነው

መጋቢት ፳፫ (ሃያ ሦስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በአዲስአበባ የመጠጥ ውሃ እና የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲሁም የሞባይልና የኢንተርኔት አገልግሎቶች መቆራረጥ በያዝነው መጋቢት ወር ተባብሶ በመቀጠሉ ነዋሪዎች ለአላስፈላጊ ኪሳራ ከመዳረጋቸው ጋር ተያይዞ በነዋሪው ዘንድከፍተኛ ምሬት መፍጠሩን ዘጋቢያችን ገልጿል።

በያዝነው  ወር የኤሌክትሪክ ኃይል ቢያንስ በሁለት ቀን አንድ ጊዜ ለሰዓታት የሚጠፋበት ሁኔታ በተደጋጋሚ መስተዋሉን ዘጋቢያችን ተዘዋውሮ ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች የገለጹ ሲሆን በዚህም ምክንያት ለአንድ ፍሬ ሻማ ወጪ ከአራት አስከ አምስት ብር ለማውጣት ተገደዋል፡፡

በተጨማሪም አንድ ጄሪካን የመጠጥ ውሃ በአንዳንድ አካባቢዎች እስከ10 ብር እየተጠየ መሆኑን የጠቀሱት ነዋሪዎች መንግስት በቴሌቪዥን የሚናገረውና በተግባር የሚታየው ሊጣጣም አልቻለም ይላሉ።

በአዲስአበባ ቦሌ፣ ገርጂ፣ 22 ማዞሪያ፣ ፒያሳ፣ ሠንጋተራ የመሳሰሉ አካባቢዎችን ጨምሮ በብዙ የከተማው ክፍሎች ውሃ በተከታታይ ከአንድ እስከ አራት ቀናት የሚጠፋባቸው አካባቢዎች መበርከታቸውን የጠቀሱት  ነዋሪዎች ሌሊት ሊመጣ ይችላል በሚል ብዙ ቤተሰቦች እንቅልፋቸውን በውሃ ጥበቃ ለማሳለፍ እየተገደዱ ነው ሲሉ አክለዋል፡፡  የወላጆችና የተማሪዎች ሥራና የትምህርት ጊዜያት በውሃ ጥበቃእየተስተጓጎለ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የሞባይል አገልግሎትን በተመለከተ አንድ ሰው በቀላሉ ደውሎ ለማግኘት የኔትወርክ መጨናነቅ ማስቸገሩን፣ ኔት ወርክ ከተገኘም በኃላ ግንኙነት ላይ እያሉ በተደጋጋሚ የመቋረጥ ችግር እንደሚያጋጥም፣ ባልታወቀ ምክንያት የያዙት ሞባይል ኔትወርኩ ዜሮ ሆኖ ከአገልግሎት ውጪ የሚሆኑባቸው ቀናት መኖራቸውን አስተያየት ሰጪዎቹ አስታውሰዋል፡፡

የኢንትርኔት አገልግሎትም በተመሳሳይ መልኩ የተዳከመ ሲሆን ጨርሶ ሚጠፋባቸው ቀናት መኖራቸውንም ጠቁመዋል፡፡አስተያየት ሰጪያችን እንደተናጋሩት EVDO በመባል የሚታወቀው ቴሌ ፈጣን ነው የሚለው የአንትርኔት አገልግሎት ትላንት ሌሊት ተቋረጦ ከ12 ሰዓታት ቆይታ በኃላ መለቀቁን እንደምሳሌ አንስተው ለዚህ ዓይነቱ ችግር የመ/ቤቱ የበላይ ኃላፊዎች ይቅርታ እንኳን ሲጠይቁ አለመሰማታቸው ለሕዝብ ያላቸውን ንቀት የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡

ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ በቅርቡ በሰጡት መግለጫ 75 በመቶ የከተማው ክፍል 24 ሰዓታት ውሃ እንደሚያገኝ፣ ቴሌ የምትታለብ ላም መሆንዋን ቢገልጹም ይህ ግን ጥራት ያለው አገልግሎት በመስጠት በተግባር አለመገለጹ እንዳሳዘናቸው ገልጸዋል፡፡

የውሃ፣የመስኖና ኢነርጂ ሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ በጥር ወር መጨረሻ ለፓርላማው ባቀረቡት ሪፖርት በተለይ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ችግር የመልካም አስተዳደር ችግር አንድ መገለጫ ነው በማለት በይፋ ያመኑ ቢሆንም ችግሩን በፈጠሩት ወገኖች ላይ የተወሰደ እርምጃም ሆነ የተስተካከለ ነገር የለም።