ኦብነግ የኦጋዴን የተፈጥሮ ጋዝ ምርትን ወደ ውጭ መላክ የማይታሰብ ነው አለ

መጋቢት ፳፩(ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኦጋዴን ነጻ አውጭ ግንባር -ኦብነግ ባወጣው ጋዜጣዊ መግለጫ ፣ የኢትዮጵያው ጠ/ሚኒስትር በበሁለት አመት ውስጥ ኦጋዴን  ያለውን የተፈጥሮ ጋዝ ለውጭ ገበያ እናቀርባለን በማለት የሰጡት መግለጫ፣  ያልተጨበጠና የማይሆን ነው ብሎአል።

መንግስት በኦጋዴን ውሰጥ ህዝቡን በጅምላ ኢላማ በማድረግ የዘር ማጥፋት ወንጀል መፈጸሙን የገለጸው መግለጫው፣ የቻይና ኩባንያ ይህን እያወቀ ለመንግስት ሰራዊትና ልዩ ሚሊሺያ እርዳታ ያደርጋል ብሎአል።

ኦብነግ ተዳክሟል እየተባለ የሚሰጠው ትንተና ትክክል አለመሆኑንም ግንባሩ ገልጿል። የሶማሌን ህዝብ መብት በመርገጥ እና ዲሞክራሲያዊ መብቱን በማፈን የክልሉን ሃብት ለመዝረፍ የሚደረገው ሙከራ በአሳዛኝ ሁኔታ ይኮላሻል ሲል አክሏል።

ግንባሩ ራሱን በደንብ የተደራጀና በጥሩ ወታደራዊ አቋም ላይ የሚገኝ መሆኑን በመግለጫው አስተዋውቋል።