እነ አቶ አንጋው ተገኝ ፍርድ ቤት ቀረቡ

ታኀሳስ ፳፩(ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፯ / ኢሳት ዜና :-ባለፈው ጥቅምት ወር በጎንደር፣ በትግራይና በጎጃም አካባቢዎች የተያዙ የተቃዋሚ ድርጅት አመራሮች ፍድር ቤት ቀርበው የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል።

ነገረ ኢትዮጵያ እንደዘገበው የሰማያዊ፣ የአንድነትና የመኢአድ ፓርቲዎች የዞን አመራሮች  ታህሳስ 21 ቀን 2007 ዓ.ም አራዳ ፍርድ ቤት ቀርበው ፣ አመራሮቹ ለ3ኛ ጊዜ የ28 ቀናት የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል፡፡ “ፖሊስ ምርመራየን አልጨረስኩም፣ የምስክር ቃል አልሰማሁም፣ ግብረ-አበሮችን አልያዝኩም በሚል ሰበብ ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው መጠየቁንና ፍርድ ቤቱም ይህንኑ መፍቀዱን ጠበቃቸው አቶ ገበየሁ ይርዳው መናገራቸውን ጋዜጣው ዘግቧል።

ጠበቃው ‹‹ፖሊስ የደንበኞቼን ቤትና ኮምፒተር በርብሮ አገኘሁ ያለውን ሰነድ ወስዶ ቃላቸውንም ከተቀበለ በሁዋላ የጊዜ ቀጠሮ የሚጠይቅበት አሳማኝ ምክንያት የለውም በማለት›› የተጠየቀውን የጊዜ ቀጠሮ ተቃውመዋል። ችሎቱ በዝግ መታየቱንና ተጠርጣሪዎቹ ‹‹በኤርትራ ሀገር ከመሸገው ግንቦት ሰባት የተባለ አሸባሪ ቡድን ጋር ግንኙነት ፈጥረዋል በሚል በሽብርተኝነት ወንጀል መከሰሳቸውን ፖሊስ ለፍርድ ቤቱ ገልጿል።

አንጋው ተገኝ፣ አባይ ዘውዱ ፣ አለባቸው ማሞ፣ ተስፋየ አላምረው፣ በላይነት ሲሳይ ፣ ተስፋየ ታሪኩና አግባው ሰጠኝ ከሁለት ወራት በፊት ታፍነው መወሰዳቸው ይታወቃል።  መንግስት ምርጫውን ተከትሎ፣ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል ህዝቡን ያደራጃሉ ብሎ የሚፈራቸውን ሰዎች ማሰሩን ኢሳት ያነጋገራቸው የተቃዋሚ መሪዎች መናገራቸው ይታወሳል።