እስረኞች በጉልበት ሰራተኝነት መሰማራታቸው ተሰማ

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 24/2010)

በአፋር ክልል በሚካሄዱ የግንባታና የማምረት ስራዎች እስረኞች በጉልበት ሰራተኝነት መሰማራታቸውን ምንጮች ለኢሳት ገለጹ።

ይህንን በአለም አቀፍ ሕግ የተከለከለው ድርጊት የሚፈጸመው ከአማራ ክልል በሚወሰዱ እስረኞች ላይ እንደሆነም ተመልክቷል።

በተለይ በዳሎል አካባቢ በፖታሺየምና በጨው ማምረት ስራ ላይ የሚገኙ የሀገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎች በእስረኞቹ ጉልበት በመጠቀም ላይ መሆናቸውን ምንጮች ለኢሳት ገልጸዋል።

በአፋር ክልል ዳሎል አካባቢ በጨውና ፖታሺየም ማምረት የተሰማሩ የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች በሺዎች የሚቆጠሩ ሰራተኞች አሰማርተዋል።

በአብዛኛው በቀን ሰራተኝነትና በኮንትራት ስራ የተሰማሩትን ሰራተኞች ከአፋር ክልልም ሆነ ከሌላ ክልል በቀላሉ ማግኘት ባለመቻሉ የአማራ ክልል እስረኞችን በአነስተኛ ገንዘብ እየተጠቀሙባቸው እንደሆነም ምንጮች ገልጸዋል።

ለእስረኞቹ የሚከፈለው ገንዘብ በትክክል ለእስረኞቹ ገቢ ስለመደረጉም የታወቀ ነገር የለም።

በስፍራው የሚንቀሳቀሱትና ያራ ኢንተርናሽናልን የመሳሰሉት ኩባንያዎች ሰራተኞቹ እስረኞች ስለመሆናቸው መረጃ ይቅረብላቸው አይቅረብላቸው የታወቀ ነገር ባይኖርም።

ከአማራ ክልል የሔዱት እስረኞች በቅርብ ክትትልና ጥበቃ ስር ሆነው በአለም አቀፍ ኩባንያዎቹ ፕሮጀክቶች ውስጥም በቀን ሰራተኝነት እያገለገሉ መሆናቸውን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

እስረኞቹ በተለይ ከሰሜን ወሎ አካባቢ የተወሰዱ እንደሆኑ የሚገልጹት ምንጮች የክልሉ መንግስትም ይሁን ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት በጉዳዩ ውስጥ ስላላቸው የተሳትፎ መጠን የታወቀ ነገር የለም።

በአፋር ክልል በጨው ማምረት ስራ ላይ የተሰማሩት የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች ከ90 በመቶ በላይ የትግራይ ተወላጆች መሆናቸውን የአፋር ሕዝብ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች በተደጋጋሚ መግለጻቸው ይታወሳል።

በአንጻሩ የአፋር ባለሃብቶች ተገፍተው እንደወጡም ያስረዳሉ።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ2009 ጀምሮ በፖታሺየም አሰሳና ቁፋሮ ላይ የነበረው ያራ ኢንተርናሽናል ከ2 ወራት በፊት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ሕዳር 7/2017 ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ባደረገው ስምምነት ወደ ስራ መግባቱም ታዉቋል።

በአመት እስከ 600 ሺ ቶን ፓታሽ በማውጣት በአካባቢው ለ20 አመታት ያህል የሚበቃ ማዕድን መኖሩን በመግለጽ ስምምነቱን የፈረመው ያራ ኢንተርናሽናል ፈሳሽ ጨው ማምረቻ እንዲሁም የፖታሽ ፕሮሰሲንግ ፋብሪካ በመገንባት ላይ መሆኑም ተመልክቷል።

በፋብሪካዎቹ ግንባታ ወቅት እስከ አንድ ሺ ያህል ሰራተኞች መሰማራታቸውም ታውቋል።

ይህ አለም አቀፍ ማዳበሪያ አምራች ኩባንያ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2005 ለአቶ መለስ ዜናዊ በሰጠው የ250 ሺ ዶላር ሽልማት ከፍተኛ ተቃውሞ እንደቀረብበት ይታወሳል።