ኢትዮጵያ መንግስት የፍትህ ሚኒስቴርን የሚያፈርስ ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ አቀረበ

ኢሳት (መጋቢት 14 ፥ 2008)

በሰብዓዊ መብቶች መከበር ዙሪያ ከተለያዩ አካላት በተደጋጋሚ ቅሬታ የሚቀርብበት የኢትዮጵያ መንግስት የፍትህ ሚኒስቴርን የሚያፈርስ ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ አቀረበ። ለበርካታ አመታት በስራ ላይ የነበረውን ይህንኑ ሚኒስቴር በምስረታ ላይ የሚገኘው የፌዴራል ጠቅላይ አቃቢ ህግ ተቋም እንደሚተካው ከሃገር ቤት የተገኘ መረጃ አመልክቷል።

በርካታ አንቀጾች እንዳሉት የተነገረለት ይኸው የፌዴራል ጠቅላይ አቃቢ ህግ ተቋም በቅርቡ በፓርላማ ከጸደቀ በኋላ የፍትህ ሚኒስቴር ህልውና እንድሚያከትም ባለስልጣናት ለመገናኛ ብዙሃን አረጋግጠዋል።

“ፓርላማው ማሻሻያውን ካጸደቀው ፍትህ ሚኒስቴር ምን ይዞ ይቆማል?” ሲሉ የፍትህ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው አምባየ ለሪፖርተር ገልጸዋል።

የፌዴራል ጠቅላይ አቃቢ ህግ ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ የህግ ማስከበር ተግባር በአቃቤ ህግ የሚከናወን መሆኑን የሚተነትን ሲሆን የፍትህና የህግ ምርምር ኢንስትቲዩቱና የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ተጠሪነታቸው አዲስ ሊቋቋም በታሰበው ተቋም ውስጥ ይሆናል ተብሏል። የፌዴራል ፖሊስም ተጠሪነቱ ለጠ/ሚኒስትሩ እንደሆነ ረቂቅ ቀርቧል።

ይኸው የፌዴራል አቃቤ ህግ ተቋም ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩና ከሚኒስቴሮች ምክር ቤት እንደሚሆን የታወቀ ሲሆን የፌዴራል ዋና ጠቅላይ አቃቤ ህግ  በፓርላማው እንደሚሾምም በረቂቅ አዋጁ መቀመጡን ከሃገር ቤት ከተገኘ መረጃ ለመረዳት ተችሏል።

ይጸድቃል ተብሎ የሚጠበቀው ይኸው አዲስ ረቂቅ አዋጅ የጸረ-ሙስና ኮሚሽን በሙስና የተጠረጠሩ ግለሰቦችን የመክሰስ ስልጣኑ ተቀንሶ መልካም ስነምግባርን በማስተማር ተግባር ላይ ብቻ እንዲያተኩር የሚያደርግ እንደሆነም ተገልጿል።

የጸረ-ሙስና ኮሚሽን ባለፉት በርካታ አመታት በመንግስታዊ ተቋማት ውስጥ የሚሰሩ ሙስናዎች በማጋለጥ ሃላፊዎችን ለህግ ሲያቀርብ መቆየቱ ይታወሳል።

ይኸው መንግስታዊ ተቋም የመንግስት ባለስልጣናት ያላቸውን ሃብት ለህዝብ ይፋ እንዲያደርጉ ከአራት አመት በፊት እንቅስቃሴን ጀምሮ የንበረ ሲሆን፣ እቅዱ ምክንያቱ ባልተገለፀ ሁኔታ እስካሁን ድረስ ተግባራዊ ሳያደርግ መቆየቱ የሚታወቅ ነው።

በቅርቡ ይቋቋማል ተብሎ የሚጠበቀው ጠቅላይ አቃቤ-ህግ በህግ ጉዳዮች የፌዴራል መንግስት ዋና አማካሪና ተወካይ ሆኖ እንደሚሰራም ተገልጿል።

ይኸው ተቋም የወንጀል ምርመራ እንዲጀመር የፌዴራል ፖሊስን ማዘዝ ጨምሮ ሌሎች በርካታ ሃላፊነቶች እንደሚኖሩትም ለመረዳት ተችሏል።