አፋኝ የተባለው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በወጣ ማግስት የጎንደር ከተማ ህዝብ የመጀመሪያውን ቀን አድማ በተሳካ ሁኔታ አደረገ

ጥቅምት ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- አስተባባሪ ግብረሃይሉ ባለፈው አርብ የጠራውን የሥራ ማቆም አድማ ተከትሎ ዛሬ የከተማ ሱቆች፣ ሆቴሎች እና አገልግሎት ተቋማት ሁሉ ተዘግተው የዋሉ ሲሆን፣ አልፎ አልፎ ከሚንቀሳቀሱ ባጃጆች በስተቀር፣ አብዛኞቹ ተሽከርካሪዎች ስራ አቁመዋል።

“ የሥራ ማቆም አድማ ማድረግ ክልክል ነው” የሚል አፋኝ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከወጣ በሁዋላ፣ አዋጁን ከምንም ባለመቁጥር በክልሉ የሥራ ማቆም አድማ ሲደረግ ከባህርዳር ከተማ አድማ ቀጥሎ ይህ ሁለተኛው ነው።

ድርጊቱ ያበሳጫቸው የሚመስሉት አገሪቱን በወታደራዊ ሃይል እየመሩዋት ያሉት የእዝ አመራሮች ፣ወታደሮቻቸው የተዘጉ የንግድ ድርጅቶችን እየሰበሩ እንዲያስከፍቱ ጥብቅ ትእዛዝ በመስጠታቸው፣ከሰአት በሁዋላ ድርጅቶችን ለማስከፈት ሙከራ ሲያደርጉ ታይቷል። ይሁን እንጅ አብዛኛው ህዝብ የሚመጣበትን ለመቀበል በመዘጋጀት የመጀመሪያውን አድማ በስኬት አጠናቋል። አገዛዙ የሥራ ማቆም አድማ ማድረግ ወንጀል ነው በማለት ያወጣው ድንጋጌ ሳምንት ሳይሞላው ባለፈው ሳምንት ባህርዳር አሁን ደግሞ ጎንደር አድማውን ማድረጋቸው አገዛዙ አፍኖ ለመግዛት የጀመረው ሙከራ እንደማይሳካ ማሳያ ነው በማለት የተቃውሞው አስተባባሪዎች ተናግረዋል።

በሌላ በኩል ኢሳት፣ ኦ ኤም ኤንንና ሌሎች የውጭ የመገናኛ ብዙሃንን እንዳይታዩ ለመከልከል ዲሾችን ለማስወረድ የሞከሩ ካድሬዎች፣ በድንጋይ ተመትተዋል። በአማራ ክልል የተለያዩ ከተሞች ወታደሮች በብዛት እየተሰማሩ ህዝቡን መግቢያ መውጫ እያሳጡት መሆኑን የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። ትጥቅ የማስፈታት እንቅስቃሴ ለመጀመር ወታደሮች ቀድሞ ዝግጅት እያደረጉ ሲሆን፣ አርሶ አደሩ ጥንቃቄ እንዲያደርግ በየአካባቢው የተሰማሩ አደራጆች አሳስበዋል።