አገር ቤት የሚገኘው ሲኖዶስ ከውጭ ከሚገኘው ጋር የተጀመረው ድርድር እንዲቀጥል ወሰነ

ጥቅምት ፳፩(ሃያ አንድ )ቀን ፳፻፮ / ኢሳት ዜና :-ቅዱስ ሲኖዶሱ ሰሞኑን ሲያደርግ የነበረውን ምልዓተ ጉበኤ ሲያጠናቅቅ ባወጣው የአቋም መግለጫ ፣ በውጭ አገር ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር ተጀምሮ የነበረው እርቀ ሰላም ወደ ፊት እንዲቀጥል እና ቤተክርስቲያን አንድነት እንዲጠናከር ወስኗል።

የኦሮቶዶክስ ሀይማኖት ተከታዮች ቆጠራ እንዲካሄድና  የቤተክርስቲያኒቷ ታሪክ በደንብ ተጠንቶ እንዲቀርብም ወስኗል። ከፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተወክለው የመጡ ሰዎች በቅርቡ ስለ አክራሪነት የሀይማኖት አባቶችን ለማስተማር በሄዱበት ወቅት ኢትዮጵያ ክርስትናን የተቀበለቸው በ4ኛው ክፍለ ዘመን ነው በማለት በመናገራቸው አባቶችን አበሳጭቶ እንደነበር መዘገባችን ይታወቃል።

ቅዱስ ሲኖዶሱ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ላይ ያለውን ነቀፋም አሰምቷል። ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ” ስለ አገራችን ጉዳይ ስንነነጋር የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የሚያቀርበው ዘገባ የጉርሻ ያክል ” ብቻ ነው በማለት፣ የሚዲያ ዘገባውን የሚፈልጉት ህዝቡ መረጃዎችን እንዲያገኝ እንጅ የሚዲያ ሱስ ኖሮባቸው አለመሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ለጉባኤው የሰጠው ሽፋን አነስተኛ መሆን በቅርቡ አንዳንድ የሀይማኖት አባቶች በመንግስት ላይ ላቀርቡት ትችት መልስ ሊሆን እንደሚችል ዘጋቢያችን ከነዋሪዎች ያሰባሰበው  አስተያየት ያመለክታል።