አንድነት ፓርቲ በምርጫ ቦርድ ላይ ያቀረበው ክስ ውድቅ ሆነ

መጋቢት ፳፫(ሃያ ሦስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ፍርድ ቤቱ በሰጠው ውሳኔ ክሱን ያቀረቡት ወገኖች የአንድነት ፓርቲን በመወከል ክስ ሊያቀርቡ አይችሉም ብሎአል። ምርጫ ቦርድ ቀደም ብሎ ህወሃት ኢህአዴግ የሰጠውን የፖለቲካ ውሳኔ ማስፈጸሙን የገለጹት

የፓርቲው የቀድሞ አመራር አቶ አስራት ጣሴ፣  የዛሬው የፍርድ ቤት ውሳኔም ህግና ደንብን የጣሰ ነው ብለዋል።

የፓርቲው የስራ አስፈጻሚ አባላት አሁንም እንዳሉ የገለጹት አቶ አስራት ፣ ሁሉንም የፍርድ ቤት ሂደቶች ካጠናቀቁ በሁዋላ፣ ተቃውሞአቸውን በሌሎች መንግዶች ሊቀጥሉ እንደሚችሉ ገልጸዋል። አቶ አስራት ጣሴ አዲስ ፓርቲ የመመስረት ሃሳብ እንደሌላቸው ገልጸው፣

ትግሉን የሚወስነው የኢትዮጵያ ህዝብና በደሉ ነው ብለዋል። ህዝባዊ አመጽ አንድ የሰላማዊ ትግል መንገድ መሆኑን የገለጹት አቶ አስራት፣ ከዚህ በሁዋላ የሚመጣውን እስከ ሞት የሚደርስ መስዋትነት ለመቀበል ዝግጁ መሆናቸውን  ተናግረዋል።

አቶ አስራት ሰላማዊ ትግልን የማይቀበሉ ህዝባዊ አመጽን ይጋብዛሉ የሚባለው ትክክለኛ አባባል መሆኑን ገልጸው፣ ህውሃት ኢህአዴጎች ወደ ህሊናቸው ተመልሰው የተካረረውን ጉዳይ ወደ ውይይት እንዲወስዱት መክረዋል።

ገዢው ፓርቲ ፍትሃዊና ነጻ ምርጫ ያካሂዳል ብለው እንደማያምኑም አቶ አስራት አክለዋል