አቶ ጁነዲን ሳዶ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ቦርድ ሰብሳቢነት ተነሱ

ታህሳስ ፬(አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ባለቤታቸው ወ/ሮ ሀቢባ ሙሀመድ ከሳውዲ አረብያ መንግስት 50 ሺ ብር እና ቅዱስ ቁራን መጽሀፎችን ተቀብለዋል ተብለው በቁጥጥር ስር ከዋሉ በሁዋላ፣ በአቶ ጁነዲን ሳዶ ላይ የሚወሰደው እርምጃ በርትቶ አሁን ደግሞ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሰቲ የቦርድ ሰብሳቢነት እንዲነሱ ተደርጓል።

አቶ ጁነዲን ከሲቪል ሰርቪስ ሚኒሰትርነታቸው ከተነሱ  እንዲሁም በኦህዴድ ውስጥ ተራ አባል ሆነው እንዲቀጥሉ ከተወሰነ በሁዋላ ነው፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የቦርድ ሰብሰቢነት ስልጣናቸውን እንዲያጡ የተደረጉት።

የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ካሳ ተክለብርሀን የዩኒቨርስቲው የቦርድ ሰብሳቢ ሆነው ተሾመዋል።

አቶ ጁነዲን ባለቤታቸው በሽብርተኝነት ወንጀል ተከሰው መታሰራቸውን በመቃወም አንድ ጽሁፍ በግል ጋዜጣ ላይ ማውጣታቸው ይታወቃል፡፡ ይህ ጽሁፍ ከስልጣናቸው ለመባረራቸው ምክንያት መሆኑን የመንግስት ቃልአቀባይ አቶ ሽመልስ ከማል በአንድ ጋዜጣ ላይ ገልጸው ነበር። የኢትዮጵያ መንግስት፣ ከሳውዲው ቢሊየነር ሼክ ሙሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲን እንዲሁም ከሳውዲ መንግስት ጋር በቅርብ እየሰራ ወ/ሮ ሀቢባ ከሳውዲ ኢምባሲ ገንዘብ በመቀበላቸው እንዴት ሽብርተኛ ሊባሉ ይችላሉ በማለት ጥያቄ ያቀረቡ የአቶ ጁነዲን ደጋፊ ኦህዴድ አባላት ከሀላፊነታቸው እየተነሱ መሆኑም ታውቋል። የኢትዮጵያ መንግስት እስካሁን የሳውዲ አረብያን መንግስትና የሳውዲ አረብያን ኢምባሲ ሽብረተኝነትን በማስፋፋት ወንጀል ሲከሳቸው አልተሰማም።