አቶ አባይ ወልዱ አቶ መለስ ዜናዊን በመተካት ሊቀመንበር ሆኑ

መስከረም ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- የህወሃት ሥራ አስፈጻሚ ሰሞኑን ባካሄደው ስብሰባ በሟቹ በአቶ መለስ ምትክ በአሁኑ ወቅት የትግራይ ክልል ፕሬዚዳንት የሆኑትንና የፓርቲው ምክትል ሊቀመንበር የነበሩትን አቶ አባይ ወልዱን ሊቀመንበር አድርጎ ሲመርጥ ኦህዴድ በበኩሉ ከህመም ጋር በተያያዘ የመልቀቂያ ደብዳቤ ባስገቡት አቶ አለማየሁ አቶምሳ ምትክ የአ/አ ከተማ ከንቲባ የሆኑትን አቶ ኩማ ደመቅሳን መምረጡን ምንጫችን ጠቁሟል፡፡
አዲሱ አመራር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝን ጠ/ሚኒስትር፣አቶ ኩማ ደመቅሳን ምክትል በማድረግ ከስድስትወር በኃላ እስከሚካሄደው የግንባሩ ጉባዔ ድረስ እንዲያገለግሉ በቅርቡ ይሾማቸዋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ አውራምባ ታይምስ እንደዘገበው፤ አቶ ሀይለማርያምን በጠቅላይ ሚኒስትርነት ከማስቀጠል ውጪ ሌላ አማራጭ ያጣው ኢህአዴግ፤ በአቶ ሀይለማርያም ሥር ሦስት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ለመሾም ወስኗል።

 

ሪፖርተር በበኩሉ በጠቅላይ ሚኒስትርነት ይመረጣሉ ተብለው የሚጠበቁት አቶ ሀይለማርያም የአቶ መለስን ያህል አቅም ስለማይኖራቸው ፤ ኢህአዴግ ከአንድ በላይ  ምክትል  ጠቅላይ ሚኒስትሮችን ሊሾምላቸው  እንደሚችል ዘግቧል።

ይሁንና የሚሹሙት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሁለት ይሁኑ አለያም ሦስት ጋዜጣው በትክክል ያስቀመጠው ነገር የለም።

 

አውራምባ እንዳስነበበው፤ሦስቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮችም፤ አንዱ ከኦሮሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት(ኦህዴድ)፣አንድ ከብሔረ-አማራ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ(ብአዴን) እና አንድ ከሕዝባዊ ወያነሀርነት ትግራይ(ህወሀት) የሚውጣጡ ናቸው።

 

በዚህም መሰረት  የኦህዴዱ አቶ ግርማ ብሩ  ተቀዳሚ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የኢኮኖሚ ጉዳዮች ሚኒስትር በመሆን  ከዘርፉ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችን ይመራሉ፤ይቆጣጠራሉ።

 

በአቶ ግርማ ብሩ ሥር ከሚሆኑት  የፌዴራል መስሪያ ቤቶች መካከል፤የማዕድንና ኢነርጂ ሚኒስቴር፣የንግድ ሚኒስቴር፣የገንዘብ ሚኒስቴር፣የ ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር፣የማዕድን ሚኒስቴር፣የትራንስፖርት ሚኒስቴር፣የኢንፎርሜሽንና ኮሚኒኬሽን ቴክኖሎጅ፣ የሳይንስና ቴክኖሎጅ እና የሀይልና የውሀ አጠቃቀም ልማት ጽህፈት ቤት ይገኙበታል።

 

አሁን የትምህርት ሚኒስትር የሆኑት የብአዴኑ አቶ ደመቀ መኮንን ደግሞ  በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ  የማህበራዊ ዘርፎችን  እንደሚመሩ ተመልክቷል።

 

የብአዴኑ አቶ ደመቀ የሚመሯቸው መሥሪያ ቤቶችም፤የትምህርት ሚኒስቴር፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ የሴቶች የወጣቶች እና  የህፃናት ጉዳዮች ሚኒስቴር፣የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስቴር እና  የፍትሕ ሚኒስቴር ናቸው።

 

ሦስተኛውና ከህወሀት የሚሾመው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደግሞ የውጪ ጉዳይና  የመከላከያና ደህንነት ጉዳዮችን  በሙሉ በበላይነት ሚቆጣጠር ይሆናል።

 

በዚህም መሰረት የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር፣የመከላከያ ሚኒስቴር፣የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና እንደ ፌዴራል ፖሊስ ያሉ በርካታ  የፌዴራል ደህንነት ተቋማት  ከህወሀት በሚወከሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ስር ይሆናሉ።

 

ይሁንና አንደ አውራምባ ዘገባ ህወሀት በቦታው ላይ የሚመድበውን ሰው አስመልክቶ ገና ስምምነት ላይ አልደረሰም።

 

ኢሳት በቅርቡ  የደረሰውን መረጃ ተንተርሶ ባጠናቀረው ሪፖርት፤ ኢህአዴግ ባልተለመደ መልኩ ከአንድ በላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮችን  ለመሾም እንደተዘጋጀ  መዘገቡ ይታወሳል።

 

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide