አቶ መላኩ ፈንታ በአንድ ትንሽ ክፍል ውስጥ ብቻቸውን መታሰራቸውን ተናገሩ

ግንቦት ፱ (ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ከሙስና ጋር በተያያዘ በእስር ላይ የሚገኙት የየኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር    አቶ መላኩ ፋንታ በእስር ቤት ውስጥ ልብቻቸው በአንድ ትንሽ ክፍል ውስጥ ከመታሰራቸውም በላይ ለአንድ ቀን ብቻ ለ10 ደቂቃ እንዲናፈሱ እንደተፈቀደላቸው ተናግረዋል። ቀኑን ሙሉ በትንሽ ክፍል ውስጥ ተዘግቶብኝ ነው የምውለው ያሉት አቶ መላኩ ፣ መንግስት ለሚያውቀው በሽታቸው የሚሆን መድሀኒትም ቢሆን ከጊዜ በሁዋላ እንደቀረበላቸው ተናግረዋል። ቤተሰቦቻቸውን እና ጠበቆቻቸውን ግን ለማግኘት እንዳልተፈቀደላቸው አስረድተዋል። የእስር ቤቱ አዛዥ በበኩላቸው አቶ መላኩ እንደማንኛውም እስረኛ መያዛቸውን ተናግረዋል።

አቶ መላኩ ሰውነታቸው ገርጥቶ እና በህመማቸው የተነሳ አጎንብሰው በመራመድ ከፍተኛው ፍርድ ቤት መቅረባቸውን በስፍራው የተገኘው ዘጋቢያችን ገልጿል።

አቶ መላኩ ያለመከሰስ መብታቸው ተገፎ መያዛቸውን በተመለከተ በጠበቃቸው ያቀረቡት አቤቱታ በፍርድ ቤቱ ውድቅ ተድርጓል።