አስራ አራት የሰብአዊ መብት ድርጅቶች ፕ/ት ኦባማ ኬንያና ኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት መሻሻል እንዲያደርጉ ጠየቁ

ሐምሌ ፲፭ (አስራአምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ድርጅቶቹ ለፕ/ት ኦባማ በጻፉት ደብዳቤ ኬንያና ኢትዮጵያ በብሄራዊ ደህንነት ስም የሚያደርሱት የሰብአዊ መብት ረገጣ ፣ አለማቀፍ ህግጋትን መጣስ ብቻ ሳይሆን፣ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የሚደረገውን ጥረት አደጋ ውስጥ እንደሚጥለው ገልጸዋል።
ደብዳቤውን የጻፉት፣ አትላንታ ካውንስል፣ ካውንስል ኦን ፎሬን ሪሌሽን፣ ሂውማን ራይትስ ፈርስት፣ ከኒይ ግራጅዌት ሴንተር እና ሲቲ ኮሌጅ ኦፍ ኒዮርክ፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የማኬን ኢንስቲቲዩት ፎር ኢንተርናሽናል ሊደርሽፕ፣ ፍሪደም ሃውስ፣ ዩናይትድ ስቴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ፒስ፣ ሂውማን ራይትስ ወች፣ ኦፕን ሶሳይቲ ፖሊሲ ሴንተር፣ ሮበርት ኤፍ ኬኔዴ ሴንተር ፎር ጀስቲስ ኤንድ ሂውማን ራይትስ፣ ጆርጅ ዋሽንግተን ዩኒቨርስቲ አነደ ጆንስ ሆፕኪንስ ሳይስ፣ ረፊዩጂ ኢንተርናሽናል እንዲሁም ሲሞንስ ኮሌጅ ናቸው።
“ኢትዮጵያና ኬንያ የአሜሪካ ወዳጅ አገራት በመሆናቸው፣ የእርስዎ ውይይትም በሰብአዊ መብት ዙሪያ ይሆናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን” ያሉ ሲሆን፣ ሁለቱም አገራት የደህንነት ስጋት ቢገጥማቸውም፣ ይህንኑ ስጋት የሲቪል ሶሳይቲ እና የነጻ ሚዲያውን ለማፈን ተጠቅመውበታል ” ሲሉ ገልጸውላቸዋል።
ፕ/ት ኦባማ በአዲስ አበባ ቆይታቸው በአፍሪካ ህብረት ጽ/ቤት ተገኝተው ንግግር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።