አርበኞች- ግንቦት 7 ለ አንድነትና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ ለ ኢትዮጰያ ህዝብ፣ ለመከላከያ ሰራዊቱና ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥሪ አቀረበ።

ጥር ፯(ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ንቅናቄው  በግንቦት 7 እና በ አርበኞች ግንባር መካከል የተደረገውን ውህደት አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ፤ << እኛ መዋሃድ መወሰናችንን  ስንገልጽ፤ በተናጠል ከሚደረጉት – በጋራ የሚደረጉ የትግል ጥረቶች ውጤታማ ይሆናሉ በሚል ብቻ ሳይሆን፣፡”የተቃዋሚ ድርጅቶች፣ በምንም ዓይነት ሁኔታ በሀገርና በሕዝብ ደረጃ ትርጉም ያለው ሥራ በጋራ መስራት አይቻሉም’ የሚለውን፣ አስከፊ ተመክሮና አመለካካት ለመስበርም ጭምር ነው።” ብሏል።

<<ከትናናሽ ድርጅቶች ዙሪያ ከሚሽከረከሩ ሀሳቦችና ስሜቶች ለመውጣትና ሀገራዊና ሕዝባዊ የሆነውን ጉዳይ ለማስቀደም የወሰነ ማንኛውም ድርጅት፣ አርበኞችና ግንቦት7፣ እንደደረሱበት የውህደት ውሳኔ ፤ወይም በሌሎች በጋራ ሊያሰሩ በሚችሉ ስምምነቶች አብሮ ለመስራት መወሰን የማይችልበት ምንም ምክንያት አይታየንም።>>ብሏል ንቅናቄው።

<<በወያኔ አድሎ ስርዓት የተንገፈገፈና ትግሉን ለመቀላቀል የቆረጠ ማንኛውም ዜጋ፣ የተገኘውን አጋጣሚ በመጠቀም ትግሉን መቀላቀል ይችላል>>ያለው አርበኞች-ግንቦት 7፤ <<የኢትዮያ ሕዝብ በአንድነት የተነሳ ቀን ደግሞ፣ የወያኔ ግብዓተ መሬት ይፈጸማል ብለን ከልብ እናምናለን።>> ሲል የመተባበርን አንድነት በ አጽንኦት ገልጿል።

ንቅናቄው ለተቃዋሚ ድርጅቶች ባስተላለፈው መልእክት <<ዛሬ በአርበኞችና በግንቦት 7፣ የተጀመረው ጉዞ ውጤታማ በመሆን ሀገራዊና ታሪካዊ ትርጉም እንዲኖረው፣ ሌሎችም በተግባር የምትንቀሳቀሱ ተቃዋሚ   ድርጅቶች፣ ወያኔን የማስወገድንና ብሎም ሀገር የማረጋጋቱን ሀላፊነት በጋራ እንድንወጣ የሚያስችል መቀራረብ እንድናደርግ ፣ በውህደት በመሰረትነው- በአርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ፣ ሥም፣ ጥሪያችንን እናቀርባለን።>> ብሏል።

ንቅናቄው ለወታደራዊና የፖሊስ ሠራዊት አባላት ባስተላለፈው መልእክት ደግሞ፤<<የወያኔን ዘረኛና አምባገነን ቡድንን ዕድሜ  ለማሳጠርና ሁላችንንም በእኩልነት የምታስተናግድ ሀገር እንድትኖር፣ የሰሞኑን ቆራጥ የዓየር ሃይል መኮንንኖች ያሳዩትን ዓርያነት በመከተልና በተገኘው አጋጣሚና ሁኔታ በመጠቀም በየቦታው የሚደረገውን ትግል እንድትቀላቀሉ በውህዱ ድርጅታችን  ሥም፣ ጥሪያችንን እናቀርባለን።>>ብሏል።

ንቅናቄው በመጨረሻም፦<<የተከበርከው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ፣በረጅም ታሪክህ አይተሄው ለማታውቀው ውርደት፣ ክፋት፣ የመከፋፈልና የመጋጨት አደጋ የዳረገህን እና  ሀገርና ሕዝብን የማራከስና የመሸጥ ዕኩይ ተግባር የተጠናወተውን  አገዛዝ ከነግብር አበሮቹ ጠራርጎ ለማስወገድ በተጀመረው የጋራ ትግል ውስጥ በቀጥታ እንድትሳተፍ አለያም  በምትችለው ቀዳዳ ሁሉ ድጋፍ እንድታደርግ፣ በአርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ ሥም፣ ጥሪያችንን እናቀርባለን።>> ሲል መግለጫውን ቋጭቷል።