አለማቀፉ የሰብአዊ መብቶች ተቆርቋሪ ድርጅት የሳውድ አረቢያ መንግስት በኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ ለተፈጸመው ጥቃት ምርመራ እንዲያደርግና እርምጃ እንዲወስድ አሳሰበ

ህዳር ፳፫(ሃያ ሦስት)ቀን ፳፻፮ / ኢሳት ዜና :-ሂውማን ራይትስ ወች ባወጣው መግለጫ የሳውዲ የጸጥታ ሀይሎችና የሳውዲ ዜጎች በኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ የሀይል እርምጃ በመውስድ ጉዳት አድርሰዋል። በኢትዮጵያውያን ሰራተኞች ላይ ለተፈጸመው ጥቃት የሳውድ አረቢያ መንግስት አስፈላጊውን  ምርመራ በማድረግ በአጥፊዎቹ ላይ ተገቢውን እርምጃ ሊወስድ ይገባል ያለው ድርጅቱ በአሁኑ ሰአት በማጎሪያ ካምፖች ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በቶሎ ወደ አገራቸው እንዲመለሱ እስከዚያው በቂ ምግብ፣ መጠለያና የህክምና አገልግሎት እንዲሰጣቸው ጠይቋል።

የሳውዲ መንግስት የጸጥታ ሀይሎች እና ዜጎች በኢትዮጵያውያን ላይ ጥቃት ከመፈጸሙ በፊት ፣ ኢትዮጵያውያንን የሚያጥላሉ ቅስቀሳዎች ይደረጉ እንደነበር ድርጅቱ አያይዞ ጠቅሷል።