ቤታቸው የፈረሰባቸው በርካታ የጎነደር ነዋሪዎች ምሬታቸውን ገለጹ

ሚያዚያ ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በዛሬው እለት አዘዞ አይራ ቀበሌ አካባቢ  ቀበሌ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች ቤታቸው በጉልበት ፈርሶባቸዋል። ነዋሪዎች ቤተሰቦቻቸውን ይዘው ሜዳ ላይ የወደቁ ሲሆን፣ በዝናብና በጸሃይ እየተቸገሩ መሆኑንም ገልጸዋል።

በነዋሪዎችና በፖሊስ መካከል መጠነኛ የሆነ ግጭት ተከስቶ እንደነበር ነዋሪዎች ተናግረዋል። አንዳንድ ነዋሪዎች ተስፋ በመቁረጥ በራሳቸው ላይ እርምጃ መውሰዳቸውን ነዋሪዎች ይገልጻሉ።

በባህርዳር ከሳምንት በፊት ከ600 በላይ ህገ ወጥ የተባሉ ቤቶች ፈርሰዋል። ቤታቸው የፈረሰባቸው ነዋሪዎች ከፖሊስ ጋር በፈጠሩት ግጭት 2 ሰዎች ሲገደሉ፣ 9 ሰዎች ደግሞ በጽኑ ቆስለዋል። ከ20 በላይ ሰዎችም በእስር ላይ ይገኛሉ።

በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች  ህገወጥ ናቸው በሚል ከሚፈርሱ ቤቶች ጋር በተያያዘ ብዙ አቤቱታዎች እየተሰሙ ነው። መንግስት ከነዋሪዎች ጋር ተነጋግሮ እርምጃ ከመውሰድ ይልቅ፣ የጉልበት አማራጭን እየተጠቀመ መገኘቱ ለሰዎች ህይወት መጥፋት መንስኤ እየሆነ ነው በማለት አንዳንድ ወገኖች አስተያየቶችን ይሰጣሉ።