በጎንደር ከተማ ከቤት ላለመውጣት የተጀመረው አድማ ለሶስተኛ ቀን ቀጥሎ ዋለ

ኢሳት (ነሃሴ 10 ፥ 2008)

በጎንደር ከተማ ከቤት ላለመውጣት የተጀመረው አድማ ለሶስተኛ ቀን ማክሰኞ መቀጠሉንና ሁሉም የመንግስትና የግል ድርጅቶች ተዘግተው እንደሚገኙ የከተማዋ ነዋሪዎች ለኢሳት አስታወቁ።

ለተለያዩ አስቸኳይ ጉዳዮች ከቤት የሚወጡ ነዋሪዎች ጥቁር ልብስን በመልበስ ብቻ የተወሰኑ እንቅስቃሴዎችን እንደሚያደርጉ እነዚሁ ለደህንነታቸው ሲሉ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ ነዋሪዎች ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ገልጸዋል።

በቅርቡ በጎንደርና እና በባህርዳር ከተሞች የተፈጸመ ግድያ በመቃወም ከቤት ላለመውጣት አድማ ላይ የሚገኙት የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች እርምጃቸው ያላቸውን ከፍተኛ ተቃውሞ የሚያሳይ እንደሆነ አስረድተዋል።

የከተማዋ አስተዳደር ባለስልጣናት ነዋሪው የተለመደ የዕለት ተዕለት የኑሮ እንቅስቃሴውን እንዲጀምር የተለያዩ ቅስቀሳዎችን ቢያደርጉም ነዋሪው በእምቢተኝነት መቀጠሉን ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

በከተማዋ የሚገኙ የጸጥታ ሃይሎች ከቆሙ ተሽከርካሪዎችና ባጃጆች ላይ ታርጋን ለመፍታት ሙከራ ቢያደርጉም የከተማዋ ነዋሪዎች የፈለጋችሁትን አድርጉ የሚል ምላሽ ሲሰጥ መቆየቱን እማኞች ለኢሳት አስታውቀዋል።

ለሶስተኛ ቀን የተጠራው ከቤት ያለመውጣት አድማ ቢጠናቀቅም፣ የተጀመረው ተቃውሞ በተለያዩ ስልቶች ቀጣይ እንደሚሆን ከኢሳት ጋር ቃለምልልስን ያደረጉ ነዋሪዎች ገልጸዋል።

ማክሰኞ ለአስቸኳይ ጉዳዮች ከቤት የወጡ ነዋሪዎች በጸጥታ ሃይሎች የተገደሉ የከተማዋ ነዋሪዎችን ለማሰብ ጥቁር ልብስ መልበሳቸውን ከነዋሪዎቹ ለመረዳት ተችሏል።

በቅርቡ በጎንደርና ባህርዳር ከተሞች ተካሄዶ በነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ከ50 የሚበልጡ ሰዎች የተገደሉ ሲሆን በተመሳሳይ ወቅት በኦሮሚያ ክልል ተካሄዶ በነበረ ተቃውሞ ከ50 የሚበልጡ ሰዎች መገደላቸውን የተለያዩ አካላት ይገልጻሉ።

የተባበሩት መንግስታትን ጨምሮ አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ግድያው በአለም አቀፍ ገለልተኛ አካል ማጣራት እንዲካሄድበት ቢጠይቁም የኢትዮጵያ መንግስት ለምርመራው ትብብር እንደሚያደርግ አቋሙን ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።

በኦሮሚያ ክልል ለወራት በቆየው ህዝባዊ ተቃውሞ ከ400 የሚበልጡ ሰዎች በተመሳሳይ የጸጥታ ሃይሎች ድርጊት ግድያ እንደተፈጸመባቸው የሂውማን ራይስት ዎች መረጃ የመለክታል።