በጉባ ላፍቶ ወረዳ በቅርቡ በተካሄደው የእስልምና ምክር ቤቶች ምርጫ ያሸነፉ ተመራጮች ዋህቢያ ናችሁ በሚል ታገዱ፣ በምትካቸውም አዲስ ምርጫ ሊካሄድ ነው

ጥቅምት ፲ (አስር) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ ዞን በጉባ ላፍቶ ወረዳ በተካሄደው የእስልምና ምክር ቤቶች ምርጫ ፣ በሳንቃ ቀበሌ ከፍተኛ የህዝብ ድምጽ አግኝተው የተመረጡት የቀበሌው የእስልምና ምክር ቤት ሰብሳቢ፣ ዋና ጸሀፊውና ሌሎች ተመራጮች የአህባሽን አስተምህሮ ይቃወማሉ፣ አህባሽን አይቀበሉም እንዲሁም በአዲስ አበባ የሚካሄደውን ተቃውሞ ለመቃወም በተጠራው ሰልፍ ላይ ለመገኘት ፈቃደኛ አልሆኑም በሚል ነው አሸናፊነታቸው ተሰርዞ በምትኩ ሌላ ምርጫ እንዲደረግ የተወሰነው።

ኢሳት ከአካባቢው ህዝብ ባገኘው ጥቆማ መሰረት ጉዳዩን ለማጣራት እንደሞከረው የእግድ ትእዛዙን ያስተላለፉት የወረዳው አስተዳዳሪ ሲሆኑ፣ እንዲታገዱ የተደረጉትም የሳንቃ ቀበሌ የእስልምና ምክር ቤት ሰብሳቢ ሼክ አህመድ ያሲን፣ ዋና ጸሀፊው አቶ ሙሀመድ ሞላ፣ የስራ አስፈጻሚ አባላት የሆኑት አቶ ኢብራሂም ሁሴንና ሼህ አሰፋ ይማም ናቸው።

ሰብሳቢው ሼክ አህመድ ያሲን መታገዳቸውን ለኢሳት አረጋግጠዋል ( 01፡00-3፡20)

በአካባቢው 25 ሰዎች ተመርጠው እንደነበር ከእነዚህም ውስጥ አምስቱ ስራ አስፈጻሚ፣ 20 ዎቹ ደግሞ የምክር ቤት አባላት ሆነው መመረጣቸውን ያስታወሱት ሼህ አህመድ ፣ ለወረዳ ምርጫ እርሳቸውና ጸሀፊያቸው ተመርጠው እንደተላኩ ተናግረዋል። በቀበሌያቸው አዲስ ምርጫ ለማካሄድ መታቀዱንም ሼክ አህመድ ገልጠዋል።

በቅርቡ በተካሄደው የመጅሊስ ምርጫ ሙስሊሙ መሪዎችን በዲሞክራሲያዊ ምርጫ እንኳን ደስ አላችሁ ለማለት እፈልጋለሁ በማለት አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ በቅርቡ በተካሄደው የፓርላማው ስብሰባ ላይ መናገራቸው ይታወሳል።

የድምጻችን ይሰማ አባላት በበኩላቸው በቀበሌዎች የመንግስት እንጅ የሀይማኖት መሪዎች ምርጫ ሊካሄድ አይችልም በማለት ምርጫውን ውድቅ በማድረግ ተቃውሞአቸውን መቀጠላቸው ይታወቃል።