በጅማ በአሰቃቂ ሁኔታ እናትና ልጅን የገደለው ወታደር በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ አልታወቀም

ኀዳር (አምስት) ቀን ፳፻፯ / ኢሳት ዜና :-ተሰድቤአለሁ በሚል ምክንያት አንድ አዛውንትን እስከ ልጃቸው በሌሊት የገደለው ወታደር ግድያውን ከፈጸመ በሁዋላ ወደ መካለከያ ካምፕ ቢያመራም ህግ ፊት ይቀርብ አይቀርብ የታወቀ ነገር የለም።

ወጣት ዮናስ በ16 ጥይቶች ተባስስቶ መገደሉን  ከቅርብ ሰዎች የተገኘው መረጃ የሚያመልክት ሲሆን ወ/ሮ መንበረም ከ10 ያላነሰ ቦታ ላይ ተደብድበው ተገድለዋል። የከተማው ህዝብ ወደ አደባባይ በመውጣት ተቃውሞውን ባሰማበት ወቅት ፖሊስ የሃይል እርምጃ በመውሰድ ህዝቡን በትኗል።

ወታደሩ የጠጣበትን ሂሳብ ሳይከፍል መውጣቱን ተከትሎ የሆቴሉ ባለቤት ልጅ ሂሳብ እንዲከፍል በጠየቀው ወቅት ተበሳጭቶና ቂም ቋጥሮ በሌሊት መሳሪያ ይዞ በመመለስ ግድያውን  ፈጽሟል። በአካባቢው የሰፈሩት ወታደሮች በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ተመሳሳይ ግድያ ሲፈጽሙ ለ3ኛ ጊዜ መሆኑን ነዋሪዎች ይናገራሉ።

ሰሞኑን ደግሞ የዳውሮኛ ሙዚቃ ተጫዋች የሆነውን ወንዴ የፌደራል ፖሊሶች ወደ ጫካ ወስደው በመደብደባቸው ግለሰቡ በአሁኑ ወቅት ሆስፒታል ተኝቷል። ድምጻዊው እግሮቹና እጆቹ መሰባበራቸውን ለማወቅ ተችሎአል። የድምጻዊውን ልጅ ወደ ካምፕ ወስደው ለሶስት ቀናት ምግብ ከልክለው እንደለቀቁት ምንጮች ገልጸዋል።

ድምጻዊው የምሽት ክለብ ያለው ሲሆን፣ በመዝናናት የነበሩ ወታደሮች የአንዲት አስተናጋጅን ሴት የእጅ አምባር ለመቀማት በመታገላቸውና ” ለምን እንዲህ ታደርጋላችሁ ብሎ በመጠየቁ መደብደቡ ታውቋል። ጅማ ትናንት ምሽት ውጥረት ሰፍሮባት ማደሩዋን  ነዋሪዎች ተናግራል።