በጀርመን የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በአማርኛ ተናጋሪዎች ላይ የደረሰውን መፈናቀል በመቃወም ፊርማ እያሳበሰቡ ነው

መጋቢት ፳፰ (ሀያ ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ኢትዮጵያውያኑ ዛሬ በጀመሩት የፊርማ ማሰባሰብ ዝግጅት ላይ በርካታ የጀርመን ዜጎች ፊርማቸውን አኑረዋል፡ ዝግጅቱን እያስተባበረ የሚገኘው የኢትዮጵያ የሲቪክና ፖለቲካ ድርጅቶች ጥምረት የተባለው ገለልተኛ ድርጅት ሊቀመንበር የሆኑት አቶ በላይ ወንድአፍራሽ ለኢሳት እንደገለጡት፣ ዝግጅቱ ለሚቀጥለው አንድ ወር ይቀጥላል።

የተሰባሰበውን ፊርማም ለጀርመን ፓርላማ፣ ለጀርመን የተለያዩ መሰሪያ ቤቶች፣ ለአውሮፓ ህብረትና፣ ለተለያዩ የአውሮፓ አገራት፣ ለአምነስቲ ኢንተርናሽናል እና ለሂውማን ራትስ ወች ይቀርባል።

ጀርመናውያን የእኛ መንግስት ይህን መንግስት የሚደግፍ ከሆነ እንቃወማለን በማለት  ፊራማቸውን ሲያስቀምጡ መዋላቸውን የገለጡት አቶ በላይ፣ “ኢትዮጵያኖች ተሰባስብን በጋራ መጣር ካችልን ለውጥ እናመጣለን” ብለዋል።

በተመሳሳይ ዜናም ” የመንግስትን ህገወጥ ድርጊት” በመቃወም በአሜሪካ ዋይት ሀውስ ፊት ለፊት ሰኞ ኤፕሪል 8. 2013 ከጣቱ 9 ሰአት ጀምሮ የተቃውሞ ሰልፍ እንደሚደረግ ታውቋል።

መንግስት ከቤንሻንጉል ጉሙዝ አካባቢ እንዲፈናቀሉ ያደረጋቸው የአማራ ተወላጆች አሁንም በከፍተና ስቃይ ውስጥ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሎአል። የቤንሻንጉል ጉሙዝ አስተዳደር በሌሎች ወረዳዎች የሚገኙ ተጨማሪ ሰዎችን ለማፈናቀል ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ለኢሳት የደረሰው ጥቆማ ያመለክታል።

ዜናው በመላ አገሪቱ ከተሰራጨ በሁዋላ ህዝቡ እየተነጋገረበት መሆኑን ከተለያዩ አካባቢዎች የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ።