በደቡብ ሱዳን ግጭቱ እንደቀጠለ ነው

ታህሳስ ፳፫( ሃያ ሦስት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በአዲሲቷ አፍሪካዊት አገር የተጀመረው የእርስ በርስ ጦርነት በሺ የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎች ህይወት ከቀጠፈ በሁዋላ የሁለቱም ተፋላሚ ሀይሎች ተደራዳሪዎች በአዲስ አበባ ቢገኙም አሁንም ጦርነቱ ቀጥሎአል።

በአዲስ አበባ ይጀመራል ተብሎ የሚጠበቀው የሰላም ድርድር የተኩስ አቋም ስምምነት እንዲፈረም ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል። የተቃዋሚው መሪ ሪክ ማቻር በበኩላቸው የተኩስ ማቆም ስምምነት ለማድረግ ዝግጁ አለመሆናቸውን ገልጸዋል።

በደቡብ ሱዳን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ልኡክ ሂልዲ ጆንሰን በአገሪቱ ያለው ጦርነት እንዲቆም ተማጽነዋል። ልኡኩ በአገሪቱ ከፍተኛ የሆነ የሰብአዊ መብት ቀውስ  መከሰቱን ገልጸዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በአገሪቱ የሚገኙ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊ ዜጎች እጣ ፋንታ አሁንም አልለየም። መንግስት በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን ወደ አገራቸው መመለሳቸው ታውቋል። ወደ አገራቸው ያልተመለሱና ከዋና ከተማዋ ውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያን እጣ ፋንታ አሁንም አልታወቀም።