በደቡብ ሱዳን የሚካሄደው ጦርነት እንደቀጠለ ነው

ታህሳስ ፳፰( ሃያ ስምንት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የመንግስትና የተቃዋሚ ደጋፊዎች በአዲስ አበባ ለድርድር ቢገኙም ቦር እየተባለ በሚጠራው አካባቢ አሁንም ከፍተኛ ጦርነት እየተካሄደ መሆኑን የሚደረሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። ሰሞኑን በተቀሰቀሰው ጦርነት ኢትዮጵያን እንደተገደሉ የሚደረሱን መረጃዎች ያመለክታሉ።

ሁለቱን ተፋላሚ ሀይሎች ፊት ለፊት በማገናኘት ጦርነቱ እልባት ያገኛል የሚል ተስፋ ቢያዝም እስካሁን ድረስ በተጨባጭ የታየ ነገር የለም። በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በሚገኙበት በዋና ከተማው ጁባ  ዳርቻዎች ከሁለት ቀናት በፊት የጦርነት ድምጽ የተሳማ ሲሆን በእነዚህ ግጭቶችና በቦር አካባቢ በሚካሄደው ከፍተኛ ጦርነት ኢትዮጵያውያን መገደላቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል። አንዳንዶች የሞቱ ኢትዮጵያውያንን ቁጥር ከ10 በታች ሲያደርሱት ሌሎች ደግሞ እሰከ 30 ያደርሱታል። ኢሳት በራሱ እና ከአለማቀፍ የመገናኛ ብዙሀንና የእርዳታ ድርጅቶች ተገደሉ የተባሉትን ኢትዮጵያውያንን በተመለከተ ለማጣራት ሙከራ ቢያደርግም አልተሳካለትም። የኢትዮጵያ መንግስትም ስለዚህ ጉዳይ ምንም ያለው ነገር የለም። አብዛኛው አገራት ዜጎቻቸውን ከደቡብ ሱዳን አስወጥተዋል፣ የኢትዮጵያ መንግስት እስካሁን በይፋ ዜጎቹን ከአገሪቱ ማስወጣት አልጀመረም። ከዚህ ቀደም ወደ 700 የሚደረሱ ኢትዮጵያውያን ከአገሪቱ ለቀው እንዲወጡ ቢደረግም እንቅስቃሴው አልቀጠለም። የመንግስት ወታደሮች ቦርን ለመያዝ በሚቀጥሉት 24 ሰአት ውስጥ በሚያደርጉት ጦርነት ከፍተኛ እልቂት ሊፈጠር ይችላል ተብሎ ተስግቷል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የአገሪቱ ነዳጅ ማውጫ በተቃዋሚዎች እጅ መውደቁን ተከትሎ በተፈጠረው ችግር፣ የሱዳኑ መሪ ፕሬዚዳንት አልበሽር ወደ ጁባ በማቅናት የነዳጅ ማውጫው በሁለቱም አገራት ጥበቃ ስር እንዲውል ስማማታቸውን ተናግረዋል።

አንድ የመንግስት ጄኔራል እሁድ እለት በተቃዋሚዎች ተገድለዋል።