በይርጋጨፌ መምህራን ለሁለተኛ ጊዜ የስራ ማቆም አድማ አደረጉ

ጥር ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ለአባይ ግድብ ማሰሪያ በሚል ያለፍላጎታቸው ደሞዛቸው የተቆረጠባቸው የይርጋ ጨፌ ሁለተኛ ደረጃ መምራህራን ከወር በፊት የስራ ማቆም አድማ ማድረጋቸውን ተከትሎ ፣ የተቆረጠባቸው ደምዞ ተመልሶ እንደሚሰጣቸው ቃል ተገብቶላቸው የነበረ ቢሆንም፣ የወረዳው አስተዳዳሪ ገንዘቡ በዝግ አካውንት የገባ በመሆኑ፣ ገንዘብ ለመክፈል አንችልም በሚል ምላሽ መስጠታቸውን ተከትሎ መምህራኑ ከትናንት ጀምሮ የስራ ማቆም አድማ አድረገዋል። አድማው ዛሬም የቀጠለ ሲሆን አስተዳደሩ ከመምህራኑ ጋር ለመነጋገር ስብሰባ ጠርተዋል። ይህን ዘገባ እስካጠናከርንብ ጊዜ ድረስ የስብሰባው ውጤት ምን እንደሆን ለማወቅ አልተቻለም።

መምህራኑ የትምህርት ጊዜውን አጠናቀው ፈተና ለመስጠት ዝግጁ በሚሆኑበት ወቅት የጀመሩት የስራ ማቆም አድማ መስተዳድሩን ማስደንገጡ ታውቋል። አንዳንድ መምህራን ስራ እንዲጀምሩ ለማባበል ባለስልጣናቱ እየተራወጡ ቢሆንም፣ መምህራኑ ግን አሻፈረን ብለዋል። ደመዞቻው እስከ ሳምንቱ መጨረሻ የማይከፈላቸው ከሆነም ሰኞ አድማውን እንደሚቀጥሉበት ገልጸዋል።

ተመሳሳይ የስራ ማቅም አድማ እድርገው የነበሩ የዲላ መምህራን የተቆረጠባቸው ደሞዝ ተመልሶ እንዲሰጣቸው በመደረጉ ስራ ለመጀመር ችለዋል። በዚህ የተበረታቱት የይርጋ ጨፌ ሁለተኛ ደረጃ መምህራን እንደ ዲላ ጓደኞቻችን ያለፈቃዳችን የተቆረጠው ደሞዝ ይመለስልን በማለት ያለፈውን አንድ ወር በስራ ላይ ሆነው ሲጠይቁ ቆይተዋል። በጉዳዩ ዙሪያ የወረዳውን ባለስልጣናት ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።