በካይሮ የፖሊስ አዛዡ ተገደሉ

መጋቢት ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በግብጽ የካይሮ ዩኒቨርስቲ አካባቢ በፈነዱ 3 ቦንቦች  አንድ የፖሊስ አዛዥ ሲገደሉ ሌሎች አምስት ሰዎችም ቆስለዋል።የጥቃቱ አላማ በፖሊሶች ላይ ማነጣጠሩን የሃገሪቱ ቴሌቪዥን ገልጿል።

የእስላማዊ ወንድማማቾች ፓርቲ ህገወጥ ተብሎ እንዲፈርስ ከተደረገና የፓርቲው ሊቀመንበርና ከዚሁ ፓርቲ በመውጣት ግብጽን ሲመሩ የነበሩት ፕሬዚዳንት ሙሀመድ ሙርሲ ከታሰሩ በሁዋላ በግብጽ ተደጋጋሚ ፍንዳታዎች እየደረሱ ነው፡፡

ወታደራዊ ስልጣናቸውን የለቀቁት ፊልድ ማርሻል ሲሲ ፕሬዚዳንት ለመሆን የሳዩት ፍላጎት ያበሳጫቸው የእስለማዊ ወንድማማቾች ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች ተቃውሞአቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው። ግብጽ ሆስኒ ሙባረክን ካስወገደችበት ካለፉት 3 አመታት ጀምሮ ሰላም እርቋት ይገኛል።

በአገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ቀውስ መከሰቱንም ዘገባዎች ያመለክታሉ።