በኢትዮጵያ የሚታየውን የኢኮኖሚ ችግር ለመቅረፍ ህዝቡን ማሳተፍ ግድ ይላል ሲሉ አንድ ታዋቂ ኢኮሚስት ተናገሩ

ሚያዚያ ፲፬ (አስራ አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በሙረይ ስቴት ዩኒቨርስቲ የኢኮኖሚክስ መምህር የሆኑት ፕሮፌሰር ሰኢድ ሀሰን ለኢሳት እንደገለጹት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚታየውን የኑሮ ውድነት ለመግታትም ሆነ የአገሪቱን የኢኮኖሚ ችግር ለመቅረፍ መንግስት ህዝቡን ያሳተፈ ስርአት መመስረት አለበት ብለዋል።

 

መንግስት ኢኮኖሚውን በበላይነት መቆጣጠሩና ከመንግስት ጋር ተለጥፈው የሚገኙት የመንግስት እና የገዢው ፓርቲ ኩባንያዎች ኢኮኖሚውን እስከ ተቆጣጠሩት ድረስ በኢትዮጵያ የሚታየውን የኢኮኖሚ ችግር መፍታት አይቻልም ብለዋል

 

በኢትዮጵያ የሚታው የኑሮ ውድነት ከአቅርቦት እጥረት ጋር በተያያዘ የመጣ መሆኑን የገለጹት ፕ/ር ሰኢድ ፣ በአግልግሎት መስክ  ካልሆነ በስተቀር በግብርናው እና ኢንዱስትሪው መስክ ምንም አይነት እድገት አለመምጣቱን ገልጸዋል። በግብርናው መስክ ምርት ያልጨመረበት ምክንያት ከመሬት ባለቤትነት፣ ከእውቀትና  ከመሬት ጥበት ጋር የተያያዘ መሆኑን ገልጸዋል

በኢትዮጵያ ውስጥ የሚታዩት የመሰረተ ልማት ግንባታዎች በአብዛኛው በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያኖች ለዘመዶቻቸው በሚልኩት እና እርዳታ ሰጪ ድርጅቶች በሚለግሱት ገንዘብ መካሄዳቸውን ፕሮፌሰሩ ገልጸዋል።

 

በኢትዮጵያ ውስጥ በአስቸኳይ የፖሊሲ ለውጥ እንደሚያስፈልግ የተናገሩት ፕ/ር ሰኢድ ፣ በተለይ  በስፋት ተንሰራፍቶ የሚገኘውን ሙስና መቆጣጠር ካልተቻለ ለኢትዮጵያ ህልውና አደገኛ መሆኑን ገልጸዋል።

 

የኢትዮጵያ ህዝብ በየጊዜው በሚንረው የኑሮ ውድነት ምሬቱን በተደጋጋሚ እንደሚገልጽ ይታወቃል።