በአዲስ አበባ በርካታ ፖሊሶች መልቀቂያ አቀረቡ

ጥቅምት ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኢሳት የፖሊስ ምንጮች እንደገለጹት አንድ የአየር ጤና የፖሊስ ባልደረባ በህክምና እጦት መሞቱን ተከትሎ፣ የክፍለከተማው ፖሊሶች ስራ በማቆም ተቃውሞአቸውን ከገለጹ በሁዋላ፣ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች ፖሊሶች መልቀቂያ አስገብተዋል።
የመቀሌ ከተማ ተወላጅ የሆነው ኦፊሰር የማነ በኩላሊት ህመም ሲሰቃይ ከቆዬ በሁዋላ፣ በፖሊስ ሆስፒታል ተገቢውን ህክምና ባለማግኘቱ፣ በግል ለመታከም 16 ሺ ብር ቢጠይቅም ለማግኘት አልቻለም። ይህን ተከትሎም ባልደረቦቹ ከሰራዊቱ አባላትና ከህዝብ ገንዘብ እንዲሰበሰብ ቢጠይቁም አመራሮቹ ፈቃደኞች ሳይሆኑ ቀርተዋል። በዚህ ውዝግብ መሃል ፖሊሱ ህይወቱ ያለፈ ሲሆን፣ የስራ ባልደረቦቹ ስራ ስራቸውን አቁመዋል።
የፖሊስ ኮሚሽነሩ ፖሊሶችን ጠርተው ያነጋገሩ ሲሆን፣” ጥጋብ ይዟችሁዋል፣ ተብታችሁዋል” የሚሉ የማስፈራሪያ ንግግር አድርገዋል። ፖሊሶቹ ግን “እኛም ብንታመም ለህይወታችን ዋስትና የለንም” በማለት የኮሚሽነሩን ማስፈራሪያ ሳይቀበሉት ቀርተዋል። ይህንን ተከትሎ በአዲስ አበባ በተለያዩ ጣቢያዎች የሚገኙ ከ20 በላይ የፖሊስ አመራሮች የስራ መልቀቂያ አስገብተዋል።ላቀረቡት የመልቀቂያ ጥያቄ ጠብቁ የሚል መልስ እንደተሰጣቸው የፖሊስ ምንጮች አክለው ተናግረዋል።