በአዲስ አበባ ስራቸውን የሚለቁ ፖሊሶች ቁጥር ከመቼውም ጊዜ በላይ ጨምሮአል

ሚያዚያ ፲፱(አሥራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከሚሰሩት ስራ ክብደት አንጻር የሚከፈላቸው ክፍያ ህይወታቸውን በአግባቡ ለመምራት እንዳላስቻላቸው የሚናገሩት ፖሊሶች፣ በገዢው ፓርቲ በኩል መፍትሄ ባለማግኘታቸው ስራቸውን ለቀው በመውጣት ላይ ናቸው። የፖሊስ እጥረት ያጋጠመው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የቅጥር ማስታወቂያ ቢያወጣም የሚመዘገብለት ሰው አላገኘም።
አንድ ፖሊስ ለኢሳት ወኪል ሲናገር፣ ከእርሱ ጋር ሰልጥነው ከተቀጠሩት ከ2 ሺ 300 ፖሊሶች መካከል ግማሽ የሚሆኑት ስራቸውን ለቀው ወጥተዋል። ሌሎቹም አማራጮችን እየፈለጉ ነው ብሎአል። ረጅም ሰአታትን በጥበቃ እንድናሳልፍ ከተደረገ በሁዋላ፣ በተጠንቀቅ ላይ ሁኑ እንባልና ልብሳችንን ሳናወልቅ 24 ሰአታት እንቆያለን ብሎአል። አንዳንዴ ምንም ነገር በሌለበት ሁኔታ በድንጋጤብቻ ፣ በተጠንቀቅ ላይ ሁኑ መባላችን ሌላው ጫና የፈጠረብን ጉዳይ ነው የሚለው ፖሊሱ፣ ከዚህም አልፎ በቂ የሆነ ምግብ እንደማያገኙና ጨማቸውን ለመቀየር እንኳን መቸገራቸውን ተናግሯል።
ስራቸውን እየለቀቁ የሚሄዱ የፌደራል ፖሊሶችና የመከላከያ አባላትም እንዲሁ ቁጥራቸው እየተበራከተ ነው። የፌደራል ፖሊስ አባላት በእያካባቢው የሚፈጠሩት ግጭቶች ከፍተኛ የሆነ የስራ ጫና እየፈጠሩባቸው በመሆኑ መንግስት ከስራቸው ጋር የሚመጣጠን ክፍያ እንዲከፍላቸው፣ የህይወትና የአካል ጉዳት ሊሚደርስባቸው የፖሊስ አባላት ተገቢው ክፍያ እንዲከፈላቸው በተደጋጋሚ ሲጠይቁ ቢቆዩም፣ አጥጋቢ መልስ እንዳላገኙ ይናገራሉ።