በአንዋር መስጊድ ዛሬም የተቃውሞ ድምጾች ተስተጋቡ

ህዳር ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ እስላም ኢትዮጵያውያን በታላቁ የአንዋር መስገድ በመገኘት በስልጣን ላይ ያለው መንግስት እየተከተለ ያለውን ፖሊሲ አምርረው ተቃውመዋል።

ምእመናኑ 27 ቁጥር የተጻፈበት ወረቀት በማውለብለብ ” አንቀጹ ይከበር፣ ኮሚቴዎቻችን ይፈቱ፣ አሸባሪዎች አይደለንም” በማለት ተቃውሞአቸውን ሲገልጹ ተሰምቷል።

ምእመናኑ 27 ቁጥር በመያዝ ተቃውሞአቸውን ያስተጋቡት በህገመንግስቱ በአንቀጽ 27 ላይ የተደነነገገው የሀይማኖት እኩልነት መብት ይከበር በማለት ነው።

አዲሱ መንግስት የመለስ መንግስት ይከተለው የነበረውን ችግሮችን በሀይል የመፍታት ዘዴ መከተሉ፣ ከኢትዮጵያውያን አልፎ በጸረ ሽብር ትግሉ ወዳጅ ተደርጋ የምትታየዋን አሜሪካ ሳይቀር እያሳሰበ የመጣ ጉዳይ ሆኗል።

በእስር ላይ በሚገኙት የኮሚቴ አባላት ላይ የሚታየው የተንዛዛ የፍርድ ሄደትና በአባላኦቹ ላይ በእስር ቤት የፈጸመው አሰቃቂ እርምጃ ምእመኑን ማበሳጨቱን ወኪላችን ከአዲስ አበባ ዘግቧል።