በአርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ የሚመራ የአርቲስቶች እና ጋዜጠኞች ቡድን የሶማሊ ክልልን ጎብኝቶ ምስክርነት ሊሰጥ ነው

ግንቦት ፳፯ (ሀያ ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የፌደሬሽን ምክር ቤት በአርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ የሚመራ  የአርቲስቶች ቡድንን እና ጋዜጠኞችን በማሰባሰብ ለአንድ ሳምንት የሚቆይ የጎብኝት መረሀ ግብር በጅጅጋ እና በሌሎች የሶማሊ ዞኖች አዘጋጅቷል።

አርቲስቶቹና ጋዜጠኞች ከትናንት ሰኞ ጀምሮ ወደ ጂጂጋ ይጓዛሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ጉብኝታቸውም ለአንድ ሳምንት እንደሚቆይ ታውቋል። የጉዞው ዋና አላማ በክልሉ የሚገኙ የጸጥታ ችግር አለባቸው የሚባሉ ቦታዎችን በመጎብኘት ልማቱ ምን ደረጃ ላይ እንደደረሰ ማየትና ለህዝቡ ማስረዳት እንዲሁም በክልሉ ውስጥ የብሄር ብሄረሰቦች መብት ምን ያክል እንደተከበረ ማረጋገጥና ለህዝብ ማስረዳት ይሆናል።

ከፌዴሬሽን ምክር ቤት የደረሰን መረጃ እንደሚያሳየው ጉብኝቱ በመጪው ህዳር ወር በሶማሊ ክልል ለሚከበረው የብሄር ብረሰቦች ቀን ሁኔታዎችን የሚያመቻች ነው። ክልሉ የጦር ቀጣና መሆኑ እንዲሁም ኢሳት በቅርቡ የክልሉ ፕሬዚዳንት በሚስጢር ያደረጉዋቸውን ንግግሮች ይፋ ማውጣቱ መንግስት በጅጅጋ ሊያደርገው ያሰበውን የብሄር ብሄረሰቦች ቀን በአል አከባበር እንዳያበላሽበት በመስጋት አርቲስቶችን ለመላክ መገደዱን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

አርቲስቶቹ እና  ጋዜጠኞቹ በሚያደርጉት ጉብኝት ክልሉ ሰላም እንደሰፈነበት፣ የብሄረሰቦች መብት እንደተከበረ ለማሳየት ምስክርነታቸውን በኢቲቪና በሌሎች የመገናኛ ብዙሀን ለህዝብ ያቀርባሉ።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ አብዲላሂ ሁሴን በፈረንጆች አቆጣጠር ጁን 13 በእንግሊዝ ጉብኝት እንደሚያደርጉ ታውቋል።

ፕሬዚዳንት አብዲላሂ በልዩ ሚሊሺያዎች አማካኝነት በኦጋዴንና እና በሌሎች የክልሉ ሰዎች ላይ በፈጸሙት ወንጀል በእንግሊዝ እንዲታሰሩ አንዳንድ ወገኖች እየጠየቁ ነው።

አቶ አብዲ ከዚህ ቀደም እንግሊዝን ለሁለተኛ ጊዜ ጎብኝተዋል። የእንግሊዝ መንግስት ለሶማሊ ክልል ልዩ ሚሊ—ሺያዎች ድጋፍ በማድረግ እንደሚወቀስ ይታወሳል።