በአለማቀፍ ድርጅቶች እርዳታ ከአንድ መቶ በላይ ኢትዮጵያውያን ከየመን ወደ አገራቸው ተመለሱ

መጋቢት ፳፱(ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-አለማቀፉ የስደተኞች ድርጅት _IOM ባወጣው ዘገባ ህይወታቸው በአደገኛ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ 131 ኢትዮጵያውያንን ከጅቡቲ ወደ አገራቸው መልሷቸዋል።

ከተመላሾቹ መካከል 100 ያህሉ ኢትዮጵያውያ ወደ የመን ለመጓዝ በዝግጅት ላይ እንደነበሩ ድርጅቱ አስታውቋል። 28 ኢትዮጵያውያን ደግሞ ከየመን ወደ ጅቡቲ በባህር ላይ ጉዞ አድርገው የደረሱ ናቸው።

በሰላም ወደ አገራቸው ከተመሰሉት መካከል አንድ እርጉዝ ሴት እና 37 ወላጅ አልባ ታዳጊዎች እንደሚገኙበት ድርጅቱ ገልጿል።

አይ ኦ ኤም በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በየመን በሚካሄደው ጦርነት የተነሳ መውጫ አጥተው እየተሰቃዩ ነው  ብሏል። ከተለያዩ መንግስታት የቀረቡለትን ጥያቄዎች ግምት ውስጥ በማስገባት ድርጅቱ 11 ሺ የሚሆኑ የውጭ አገር ዜጎችን ከየመን ለማውጣት

እንቅስቃሴ እንደሚጀምርም አስታውቋል። አንዳንድ አገሮች በየመን ላይ ያየር ጥቃት ከምትፈጽመዋ ሳውዲ አረቢያ ፈቃድ እየጠየቁ ለተወሰኑ ሰአታት አውሮፕላን እየላኩ ዜጎቻቸውን ለማስወጣት ችለዋል።

የኢህአዴግ መንግስት ኢትዮጵያውያኑን የማስወጣቱን ሃላፊነት ለአይ ኦ ኤም ሳይሰጥ እንዳልቀረ ምረጃዎች ያመለክታሉ።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሃኖም በቻይና የባህር ሃይል ሰራተኞች ድጋፍ ወደ አገራቸው የገቡ 30 ሰዎችን ” የመጀመሪያው ዙር ስደተኞች ወደ አገራቸው ገብተዋል” ብለው ከሳምንት በፊት ቢያስታውቁም፣ ከዚያ በሁዋላ መስሪያ ቤታቸው ያለው ነገር የለም።