በናይጀሪያ-አቡጃ በሚገኝ አንድ አውቶቡስ ማረፊያ በደረሱ ሁለት የቦንብ ፍንዳታዎች ከ 40 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ቢቢሲ ሰገበ።

ሚያዚያ ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የቢቢሲዋ ወኪል  ሀሩና ታንጋሳ ከአቡጃ እንዳጠናቀረችው ሪፖርት ፤ፍንዳታዎቹ የተከሰቱት የትራፊክ መጨናነቅ በነበረበት  ሰዓት ሲሆን፣ አብሳኞቹ ሟቾች እና ተጎጂዎች ወደ ሥራ ለመግባት አውቶቡስ እና ታክሲ ለመሳፈር ከቤታቸው ማልደው የሚገሰግሱ ነበሩ።

የዓይን ምስክሮች የበርካታ ሟቾች አስከሬን ጎዳናውን ሞልቶት ማየታቸውን ገልጸዋል።  ጥቃቱን የፈፀመው “ቦኮ ሀራም” የተሰኘው  የእስላሚስት ሚሊሺያ ቡድን ሳይሆን እንዳልቀረ ተገምቷል።

ባዳምሲ ኒያንያ  የተባሉ የ ዓይን ምስክር  በ ዓይናቸው  የ አርባ ሟቾችን አስከሬኖች እንደተመለከቱ -ለሴና አውታሩ ገልጸዋል። ሌላ የዓይን ምስክርም፤ የአደጋ መከላከል ሠራተኞችና ፖሊሶች የሟቾችን አስከሬኖች ሲያነሱ ማየየታቸውን ገልጸዋል። ፍንዳታው የተከሰተው ከከተማው ሴንተር 16 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው  በኒያና ሞተር ፓርክ  ሲሆን፤ቦንቦቹ ተጠምደው የነበሩት ከምድር በታች በአንድ ሜትር ተኩል ጥልቀት ነበር።

ሁለተኛው ፍንዳታ የነዳጅ ማጠራቀሚያ “ታንክ”ን  በማጋየቱም፤ በሰው ህይወት ላይ ከደረሰው ጉዳት በተጨማሪ በፓርኩ ከነበሩ መኪኖች ከ30 በላይ የሚሆኑት መጋየታቸውን አሲሺየትድ ፕሬስን በመጥቀስ ቢቢሲ ጨምሮ ሰግቧል ።

አደጋውን ተከትሎ በስፍራው የደረሱ አምቡላንሶች የሟቾችን አስከሬን እና ተጎጅዎችን በአቅራቢያ ወደሚገኝ ሆስፒታል ወስደዋል።