በተለያዩ ወንጀሎች የተከሰሱ ፍርድ ቤት ቀርበው የደረሰባቸውን ስቃይ ተናገሩ

ኀዳር ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በእነ ዘላለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ የተከሰሱት አቶ ባህሩ ደጉ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደተፈጸመባቸው ለፍርድ ቤቱ ያቀረቡ ሲሆን፣ በምርመራ ወቅት በግዳጅ ቃላቸውን እንዲሰጡ በመርማሪዎቹ መደረጋቸውንና እራቁታቸውን መደብደባቸውን ከድብደባ ብዛት የተነሳም ሽንታቸውን መቆጣጠር እንደተሳናቸውና የራሳቸውን ሽንት እንዲጠጡ በመርማሪዎች መደረጋቸውን ለፍርድ ቤቱ ተናግረዋል።
” አቶ ባህሩ የግንቦት 7ቱ መሪ ብርሃኑ ነጋ ምንህ ነው? ከአንዳርጋቸው ጽጌስ ጋር ምን ግንኙነት አለህ? ብርሃኑ ዘመድህ ነው?” የሚሉ ተደጋጋሚ ጥያቄዎች እያቀረቡ በማያውቁት ነገሮች ሲሰቃዩ እንደነበር ለችሎቱ አስረድተዋል።
አቶ ባህሩ ደጉ በማነታቸው ምክንያትም ጥቃት እንደደረሰባቸው ለፍርድ ቤቱ ያስረዱ ሲሆን፣ የመጣሁበት አካባቢ ህዝብ እየተሰደበና እየተዋረደ ፣ የደም ስርህን በጥሰን እንገልሃለን፤ ፖሊሱ፣ አቃቤ ህጉ፣ ፍርድ ቤቱ፣ ደህንነቱ ሁሉም የኛ ነው አንተን ከፈለግን 20 ዓመታት እናስርሃለን በማለት ዛቻና ምስፈራሪዎች እንደተፈጸመባቸው ገልጸዋል።
በምርመራ ወቀት የሰጡት የእምነት ክህደት ቃል በግዳጅ የሰጡት መሆኑን ፍርድ ቤቱ እንዲያውቅላቸው አሳስበዋል። በሕገመንግስቱ በኃይል የተሰጠ መረጃ እንደመረጃ ስለማይቆጠር ይህ ከግምት ውስጥ እንዲገባም ጠይቀዋል።
9ኛው ተከሳሽ አቶ ባህሩ ደጉ ሦስት መከላከያ ምስክሮችን አሰምተዋል። 1ኛ ተከሳሽ ዛላለም ወርቃገኘሁ እና ጦማሪ ዘላለም ክብረት ተከሳሹ ለሽብር ወንጀል ስልጠና ሊወስድ ነበር በሚል ስለቀረበበት ክስ የስልጠናውን አይነትና የአሰልጣኞችን ማንነት በማብራራት ስልጠናው ለሽብርተኝነት ድርጊት ሳይሆን በታወቁ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች የሚሰጥ ግልጽ ስልጠና እንደነበር አስረድተዋል፡፡
3ኛ ምስክር በበኩላቸው ተከሳሹ ማዕከላዊ ወንጀል ምረመራ በነበረበት ወቅት አብረው ታስረው እንደነበር በመግለጽ ይፈጸምበት የነበረውን አሰቃቂ ምርመራ በተመለከተ የሚያወቁትን መስክረዋል፡፡ እኒህ ምስክር ተከሳሹ ሌሊት ለምርመራ በሚል እየተጠራ ድብደባ ይፈጸምበት እንደነበር አስረድተዋል፡፡
በዚሁ መዝገብ 1ኛ ተከሳሽ በምስክርነት የጠሯቸው አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ የሺዋስ አሰፋ እና ዳንኤል ሺበሽ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንዲቀርቡ በተደጋጋሚ ትዕዛዝ ከፍርድ ቤቱ ቢሰጥም እስካሁን አለመቅረባቸው ታውቋል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ ዛሬም ሌላ ትዕዛዝ በመስጠት ማረሚያ ቤቱ እስካሁን ያላቀረበበትን ምክንያት ገልጾ በቀጣይ ቀጠሮ እንዲያቀርባቸው ታዝዟል ሲል ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል።
በተመሳሳይ የፍርድ ቤት ዜና ደግሞ የልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛው ችሎት በነ ዘመነ ምረቱ ላይ አቃቢ ህግ ምስክሮችን አሰምቷል።
አንደኛው ምስክር “አቶ ዘመነ ምረቱ መስከረም 18/07 በመራው ስብሰባ ላይ “መንግስትን መጣል አለብን፣ እኛ አመፁን ማነሳሳት አለብን ፣ ተማሪውን ነጋዴውን እንዲሁም አርሶ አደሩን ማብቃት አለብን፣ አርበኞች ግንቦት 7 በሚገባ ያስታጥቁናል፣ እኛም በቻልነው አቅም ሁሉ ማሸበር አለብን ። አየር ኃይሉን በመክዳት ግንቦት ሰባትን የተቀላቀሉ 4አብራሪዋች አንድ ሊኮፍተር ይዘው ሂደዋል እና እኛ መበርታት አለብን ” ብሎአል ሲል የተጠና ምስክረነቱን ሰጥቷል።
በመቀጠል ጥር10/07 በተደረገው ስብሰባ ላይ አቶ ዘመነ የወረዳው አመራሮች ፊት “እኛ ምርጫ አንገባም ፣ ወያኔ በምርጫ አይለቅም የሚበጀን እውጭ ያሉት አንድ እየሆኑ ነው እኛም አገር ውስጥ ያለነው አንድ መሆን አለብን ” ብሎ ስብሰባው ሲጨርስ ” ቦምብ” ሰጠኝ ብሎአል።
መስካሪው በቀረረበት የመስቀለኛ ጥያቄዎች ፣ የሚሊሺያ ዘርፍ አባል መሆኑን አምኗል። ግለሰቡ ታስሮ እንደነበርና በእሱ ላይ ለመመስከር ሲል መፈታቱንም በመስቀለኛ ጥያቄው አምኗል።
2ኛ ምስክር ደግሞ በጌትነት ደርሶ ላይ መስክሯል። ምስክሩም ” ግንቦት7ትን ተጠቅመን ከአገር ለመውጣት በመፈለጋችን ድርጅቱን ተቀላቅለናል ያለ ሲሆን ፣ ከአገር ለመውጣት ግንቦት7ትን መምረጥ ለምን አስፈለገ ሲባል” ሌላ አማራጭ ስለሌለ” የሚል መልስ ሰጥቷል።
ጌትነት በቀቀረበበት ክስ ላይ መልስ እንዲሰጥ ሲጠየቅ “እኔ የምናገረው ይህ አምባገነን ስርአት በህዝብ ሲቀየር ለእውነተኛው የህግ ዳኛ እናገራለሁ፣ አሁን ግን ምንም የምናገረው የለኝም፣ ወያኔ ነፈሰ ገዳይ ነው እናንተም አስፈፃሚ ናችሁ ” የሚል መልስ ሰጥቷል። አቶ ዘመነ ምህረት የመኢአድ ም ክትል ፕሬዝደንት ነው።
አሁንም ከፍርድ ቤት ዜና ሳንወጣ በሀሰት አልመሰክርም ብሎ በእስር በመሰቃየት ላይ ያለው ሙጂብ አሚኑ በተከሰሰበት ክስ እንዲከላከል ተወሰኖበታል። ሙጂብ በእነ ኤልያስ ከድር የክስ መዝገብ በተከሰሱት ላይ በሃሰት እንዲመሰክር ሲጠየቅ አሻፈረን በማለቱ ለከፍተኛ ስቃይ ተዳርጎ ቆይቷል። የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት ሙጂብ ክሱን እንዲካለከል ወስኖ ለጥር 23 ቀን 2008 ዓም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ በቃሊቲና ቂሊንጦ እስር ቤቶች ድንገተኛ ፍተሸ ሊደረግ መሆኑ ታውቋል።
በጎንደር እስር ቤት መቃጠሉን ተከትሎ ከ20-እስከ 30 የሚጠጉ እስረኞች ማለቃቸውንና በመቶዎች የሚቆጠሩት ደግሞ ማምለጣቸውን ተከትሎ ፣ በአዲስ አበባ በተለይም በቂሊንጦና ቃሊቲ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ድንገተኛ ፍተሻ ሊደረግ መታሰቡን ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ከአሁን ቀደም በሁለቱ እስር ቤቶች ድንገተኛ ፍተሻ የተደረገ ሲሆን፣በተለያዩ ጊዜያት በተለይም በፖለቲካ ጉዳይ የታሰሩትን ኢትዮጵያውያን ለይተው በመፈተሽ ቁሰቁሶቻቸውን ወስደውባቸዋል፡፡በተደጋጋሚ በፍተሻ ቁሳቁሶቻቸው ከተወሰዱባቸው መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና አንዱ ዓለም አራጌ የሚጠቀሱ ሲሆን፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ መፅሃፍ ቅዱሱን ሳይቀር ተነጥቋል።
የጎንደር እስር ቤት ተቃጥሎ እስረኞቹ በማምለጣቸው በሌሎች እስር ቤቶች በተለይም በፖለቲካ ጉዳይ ሽብርተኛ እየተባሉ የተከሰሱ እስረኞች የሚበዙባቸው ቃሊቲና ቂሊንጦም ላይ ተመሳሳይ ችግር ይፈጠራል ተብሎ በመሰጋቱ ፣ ቅዳሜ ህዳር 25ና እሁድ ህዳር 26/2008 ዓ.ም ለሁለት ቀን ከሌሊቱ 11 ሰዓት ጀምሮ ድንገተኛ ፍተሻ ሊደረግ እንደሚችል የውስጥ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ፍተሻው አሁንም በፖለቲካ ጉዳይ በታሰሩት ላይ ትኩረት እንደሚኖረው የተገመተ ሲሆን፣ እስር ቤቱ ላይ ቃጠሎ በማስነሳት ሊያመልጡ ይችላሉ የሚል ስጋት መፈጠሩም ታውቋል፡፡